
ደብረ ማርቆስ: ሐምሌ 24/2017 ዓ.ም (አሚኮ) በምሥራቅ ጎጃም ዞን ዞናዊ የአንድ ጀንበር የችግኝ ተከላ መርሐ ግብር በአነደድ ወረዳ አምበር ከተማ እየተካሄደ ነው።
የዞኑ ግብርና መምሪያ ኀላፊ አበበ መኮንን በአንድ ጀንበር የችግኝ ተከላ መርሐ ግብር እየተካሄደ መኾኑን ገልጸዋል።
ባለፉት ዓመታት የተተከሉ ችግኞችን የመንከባከብ ባሕል እያደገ መምጣቱን የተናገሩት ኀላፊው የተተከሉ ችግኞችን ተንከባክቦ የሚጠበቅባቸውን ጠቀሜታ እንዲሰጡ ሁሉም የማኅበረሰብ ክፍል የበኩሉን ሚና ሊወጣ እንደሚገባ አሳስበዋል፡፡
የምሥራቅ ጎጃም ዞን ብልጽግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት የአደረጃጀት ዘርፍ ኀላፊ ሙሉቀን ቢያድግልኝ ማኅበረሰቡ የሚተክላቸውን ችግኞች በባለቤትነት ተረክቦ መንከባከብ እና እንዲጸድቁ ማድረግ ይጠበቅበታል ብለዋል፡፡
የአነደድ ወረዳ ዋና አሥተዳዳሪ አየለ ድረስ በወረዳው “በመትከል ማንሰራራት” በሚል መሪ ሃሳብ የችግኝ ተከላ መርሐ ግብር ሲከናወን መቆየቱን ተናግረዋል።
በመርሐ ግብሩ ላይ የተገኙት የወረዳው ነዋሪዎችም በአንድ ቀን የችግኝ ተከላ ታሪካዊ መርሐ ግብር ላይ መሳተፋቸው እንዳስደሰታቸው ገልጸዋል። ለችግኞች ተገቢውን እንክብካቤ እንደሚያደርጉም ተናግረዋል።
በአነደድ ወረዳ በተካሄደው ዞናዊ የአንድ ቀን የችግኝ ተከላ መርሐ ግብር የዞኑ ከፍተኛ የመንግሥት የሥራ ኀላፊዎች እና የተለያዩ የማኅበረሰብ ክፍሎች ተሳትፈዋል።
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
👇👇👇
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!