
ባሕር ዳር: ሐምሌ 24/2017 ዓ.ም (አሚኮ) ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ በጅግጅጋ ከተማ በአንድ ጀንበር የአረንጓዴ አሻራ መርሐ ግብር አሻራቸውን አሳርፈዋል።
በመርሐ ግብሩ ላይ መልዕክት ያስተላለፉት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ የዛሬው ቀን ኢትዮጵያውያን 700 ሚሊዮን ችግኝ ለመትከል የሚረባረቡበት ታሪካዊ ቀን ነው ብለዋል።
በአረንጓዴ አሻራ መርሐ ግብር በሚቀጥለው ዓመት 50 ቢሊዮን ለመድረስ እየተሠራ መኾኑንም ተናግረዋል። በመጀመሪያው ዓመት የተክልናቸው ፍራፍሬዎች ፍሬ እየሰጡ ነው ብለዋል። ከተጠቃሚነት ጋር የማያያዝ ሥራ እንደሚቀጥልም ገልጸዋል።
የአረንጓዴ አሻራ መርሐ ግብር የኢትዮጵያ የማንሰራራት ዘመን ነው በሚል እየተከናወነ መኾኑን ነው ያነሱት። ዘንድሮ የኢትዮጵያ የማንሰራራት ዘመን መነሻ መኾኑንም ተናግረዋል።
የኢትዮጵያ የዘንድሮው ዕድገት ስኬታማ መኾኑንም ገልጸዋል። በሚቀጥለው ዓመትም እድገታችን እናስቀጥላለን ነው ያሉት። በአንድ ጀንበር የአረንጓዴ አሻራ መርሐ ግብር በምሥራቋ የወርቅ ምድር ሶማሌ ክልል ጅግጅጋ እየተከልን ነው ብለዋል።
የሶማሌ ክልል በግብርና ዘርፍ ትልልቅ ሥራ እየሠራ መኾኑንም ተናግረዋል። የጅግጅጋ ከተማም በከፍተኛ ደረጃ እያደገች መኾኗንም ተናግረዋል።
የአንድ ጀንበር የአረንጓዴ አሻራ መርሐ ግብራችን ዕቅዳችን እናሰካለን ያሉት ምክትል ጠቅላይ ሚኒሰትሩ ሁሉም ቦታ ላይ ትልቅ መነቃቃት አለ፣ ሕዝቡ በጣም ታታሪ፣ መንግሥትን የሚያዳምጥ፣ የሚጠቅመውን ነገር የሚሠራ ሕዝብ ነውና ይህን ታታሪነታችን ዛሬ እናስመሰክራለን ነው ያሉት።
ዛሬ 700 ሚሊዮን ችግኝ ሳንተከል መተኛት የለም፣ እንቅልፍም አይወስደንም ብለዋል በመልዕክታቸው።
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
👇👇👇
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!