
ባሕር ዳር: ሐምሌ 24/2017 ዓ.ም (አሚኮ) በአንድ ጀምበር የ700 ሚሊየን ችግኝ ተከላ መርሐ ግብር ኢትዮጵያውያን በመላው ሀገሪቱ ከንጋቱ 12:00 ሰዓት ጀምሮ በነቂስ በመውጣት አሻራቸውን ማኖር ጀምረዋል።
ላለፍት ስድስት ዓመታት 40 ቢሊየን ችግኝ የተከለችው ኢትዮጵያ ዘንድሮም 7 ነጥብ 5 ቢሊየን ችግኝ ለመትከል የቅድመ ዝግጅት ሥራዎች ሲሰራ ቆይቷል።
ኢትዮጵያውያን ባለፉት ዓመታት በአንድ ጀንበር የችግኝ ተከላ መርሐ ግብርም የነቃ ተሳትፎ በማድረግ የራሳቸውን ክብረወሰን በየዓመቱ በማሻሻል ታሪክ ሰርተዋል።
የዘንድሮው የአንድ ጀንበር የችግኝ ተከላ መጀመርን አስመልክቶ መግለጫ የሰጡት የመንግሥት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት ሚኒስትር ድኤታ ተስፋሁን ጎበዛይ የመቻል አቅማችንን የምናሳይበት ነው ብለዋል።
ለዓለም አካባቢ ጥበቃ ከፍተኛ አበርክቶን እየተወጣች ያለችው ኢትዮጵያ በዘንድሮው መርሐ ግብርም አዲስ የታሪክ ምዕራፍ ለመጻፍ ተዘጋጅተናል ብለዋል።
የችግኝ ተከላ ቦታዎች ላይ የግብርና ባለሙያዎች እንደሚገኙ የተናገሩት ሚኒስትር ደኤታው እንዳለፉት ዓመታት ሁሉ የመትከያ ቦታዎች በጂኦ ሪፈረንስ ተደግፈው ወደ አንድ የመረጃ ማደራጃ ማዕከል የመረጃ ቋት ይላካሉ ብለዋል።
ኢትዮጵያውያንም በነቂስ በመውጣት ታሪካዊ ኀላፊነታቸውን እንዲወጡም ጥሪ አቅርበዋል።
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
👇👇👇
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!