
አዲስ አበባ፡ ሐምሌ 22/2017 ዓ.ም (አሚኮ) የአዲስ አበባ ከተማ አሥተዳደር ኮሙኒኬሽን ቢሮ ሠራተኞች የአረንጓዴ አሻራ ችግኝ ተከላ አካሂደዋል።
በ7ኛው ዙር የአረንጓዴ አሻራ መርሐ ግብር የመንግሥት ሠራተኞችን ጨምሮ መላው ኢትዮጵያውያን ኢኮኖሚያዊ እና ሥነ ምህዳራዊ ፋይዳ ያላቸው ችግኞችን እየተከሉ ነው።
የአዲስ አበባ ከተማ አሥተዳደር ኮሙኒኬሽን ቢሮ ሠራተኞች “በመትከል ማንሰራራት” በሚል መሪ መልዕክት በመዲናዋ የአረንጓዴ አሻራቸውን አሳርፈዋል።
በችግኝ ተከላ መርሐ ግብሩ የተገኙት የአዲስ አበባ ከተማ አሥተዳደር ከንቲባ አዳነች አቤቤ ችግኝ መትከል የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ እና የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል የሚያስችል ነው ብለዋል።
“ዛሬ ላይ የምንተክለው ችግኝ ለነገው ትውልድ የምናስረክበው ገጸ በረከት ነው” ብለዋል።
እያንዳንዱ ዜጋ ችግኝ ከመትከል ባሻገር ሌሎችም ችግኞችን እንዲተክሉ እና እንዲንከባከቡ ሀገራዊ ኀላፊነታቸውን እንዲወጡ መሥራት እንደሚገባም ከንቲባዋ አስገንዝበዋል።
በመርሐ ግብሩ የሚዲያና ኮሙኒኬሽን መሪዎች፣ ባለሙያዎች፣ ታዋቂ ግለሰቦች እና የማኅበራዊ ሚዲያ አንቂዎች ተሳትፈዋል።
ዘጋቢ፦ ቴዎድሮስ ደሴ
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን