
አዲስ አበባ፡ ሐምሌ 21/2017 ዓ.ም (አሚኮ) የማዕድን ሚኒሥቴር ከ350 ሚሊዮን ብር በላይ ግምት ያላቸው ተሽከርካሪዎችንና ኮምፒተሮችን ለክልሎች ድጋፍ አድርጓል።
ድጋፉን ያስረከቡት የማዕድን ሚኒሥትሩ ኢንጂነር ሀብታሙ ተገኘ በክልሎች ያለውን የተሽከርካሪ እጥረት ለመፍታት ሚኒሥቴር መሥሪያ ቤቱ በየጊዜው ድጋፍ እያደረገ መኾኑን አንስተዋል።
በዛሬው ዕለትም ሚኒሥቴር መሥሪያ ቤቱ ከ350 ሚሊዮን ብር በላይ ወጭ የተደረገባቸው 29 ተሽከርካሪዎችን እና 81 ኮምፒተሮችን ድጋፍ ማድረጉን ነው ሚኒሥትሩ የገለጹት።
ሚኒሥቴር መሥሪያ ቤቱ ባለፈው በጀት ዓመት የተለያዩ ማዕድናትን ለውጭ ገበያ በመላክ አበረታች ለውጥ ማስመዝገቡን ጠቁመዋል።
ዛሬ የተደረገው ድጋፍም በዘርፉ የተገኘው ውጤት ቀጣይነት እንዲኖረው እና ጸጋዎችን በአግባቡ ለመጠቀም እንዲያስችል ነው ብለዋል።
ድሬድዋ ከተማ አሥተዳደርን ጨምሮ ለ12 ክልሎች የማዕድን ቢሮዎች ድጋፍ መደረጉን የገለጹት ሚኒሥትሩ ከክልሎች በተጨማሪ ለሁለት ተጠሪ ተቋማት ማለትም ለኢትዮጵያ ጆኦሎጅካል ኢንስቲትዩት እና ለማዕድን ኢንዱስትሪ ልማት ኢንስቲትዩት ድጋፍ መሰጠቱንም ተናግረዋል።
ዘጋቢ፦ ቴዎድሮስ ደሴ
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
👇👇👇
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!