አልማ በታች አርማጭሆ ወረዳ ያስገነባቸውን ሁለት የመማሪያ ሕንጻዎች ለአገልግሎት ክፍት አደረገ።

17

ጎንደር: ሐምሌ 19/2017 ዓ.ም (አሚኮ) ሕንፃዎቹ ስምንት የመማሪያ ክፍሎችን የያዙ ሲኾኑ ከ6 ሚሊዮን ብር በላይ ወጭ እንደተደረገባቸው የጎንደር አካባቢ አልማ ማስተባበሪያ ጽሕፈት ቤት ዳይሬክተር ደረጀ ዘውዴ ተናግረዋል።

ተቋማቸው ‎በበጀት ዓመቱ 160 ሚሊዮን ብር ከአባላቱ መሰብሰቡን የጠቀሱት ዳይሬክተሩ በ2017 ዓ.ም 40 መማሪያ ክፍሎች መጠናቀቃቸውን ተናግረዋል።

ዳይሬክተሩ ‎ቀሪ 102 የመማሪያ ክፍሎችን ደግሞ እስከ ነሐሴ መጨረሻ እንደሚጠናቀቁ አንስተዋል።

‎በባለፉት አምስት ዓመታት በለውጥ እቅዱ 148 ፕሮጀክቶችን ማከናወን መቻሉንም ዳይሬክተሩ አብራርተዋል። ‎በመኾኑም 441 ሺህ 877 የኅብረተሰብ ክፍሎችን ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉን ነው ያስረዱት። አልማ በሠራቸው ፕሮጀክቶች ከ39 ሺህ በላይ ለሚኾኑ ዜጎች የሥራ እድል መፈጠሩንም ዳይሬክተሩ አብራራተዋል።

‎አልማ ከመደበኛ አባላት ባሻገር ከአጋር አካላት ጋር በመቀናጀት ግንባታዎች፣ ሥልጠናዎች፣ ለትምህርት ቤቶች እና ለጤና ተቋማት የቁሳቁስ ድጋፍ እያደረገ እንደሚገኝ ተናግረዋል።

‎ለትምህርት እና ለጤና ተቋማት የቁሳቁስ ድጋፍ በተቋሙ ከ102 ሚሊዮን ብር በላይ ወጭ መኾኑም ተገልጿል።

ዛሬ ከተመረቁት በተጨማሪ አልማ ‎በታች አርማጭሆ ወረዳ 10 መማሪያ ክፍሎችን የያዘ ባለ አንድ ፎቅ የመማሪያ ክፍል እየተሠራ መኾኑ ተጠቅሷል። በሳንጃ ከተማ የቅድመ አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት የመሠረት ድንጋይ መቀመጡም ተጠቅሷል።

‎በመርሐ ግብሩ ላይ የተገኙት የታች አርማጭሆ ወረዳ ዋና አሥተዳዳሪ አስማረ የኋላሸት አልማ በወረዳው በትምህርት፣ በጤና እና በሌሎች ዘርፎች እየሠራ ያለው ተግባር የሚበረታታ ነው ብለዋል።

‎የማዕከላዊ ጎንደር ዞን ትምህርት መምሪያ ኀላፊ ክንዱ ዘውዱ የተመረቁ የመማሪያ ክፍሎች የትምህርት ጥራትን ለማሻሻል ጉልህ ሚና እንደሚኖራቸው አንስተዋል።

‎በዞኑ እየተሠሩ ያሉ የአልማ ፕሮጀክቶችን ለማብዛት የአባላትን ቁጥር መጨመር እንደሚያስፈልግ የተናገሩት ደግሞ የማዕከላዊ ጎንደር ዞን ምክትል አሥተዳዳሪ እና መሬት መምሪያ ኀላፊ አላምረው አበራ ናቸው።

‎የተጀመሩ የልማት ሥራዎችን በተያዘላቸው የጊዜ መርሐ ግብር ለማጠናቀቅ ሰላም ቀዳሚ ተግባር በመኾኑ ማኅበረሰቡ ለዘላቂ ሰላም እንዲሠራም መልዕክት አስተላልፈዋል።

ዘጋቢ :- አዲስ ዓለማየሁ

የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
👇👇👇
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation

ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!

Previous articleየፋይናንስ ዘርፉ ዘመናዊ እና ተወዳዳሪ እንዲኾን ደንበኞች ላይ ትኩረት ያደረገ የባንክ አገልግሎት መስጠት ያስፈልጋል።
Next article“6 ነጥብ 7 ሚሊዮን ኩንታል ምርት ለውጭ ገበያ ማቅረብ ተችሏል” ርእሰ መሥተዳድር አረጋ ከበደ