
ባሕር ዳር፡ ሐምሌ 19/2017 ዓ.ም (አሚኮ) የአማራ ክልል ምክር ቤት 6ኛ ዙር፣ 4ኛ ዓመት የሥራ ዘመን፣ 10ኛ መደበኛ ጉባኤውን እያካሄደ ነው።
የአማራ ክልል ርእሰ መሥተዳድር አረጋ ከበደ የመንግሥትን የ2017 በጀት ዓመት የሥራ አፈጻጸም እያቀረቡ ነው።
በሪፖርታቸውም በከተሞች ላይ የኮሪደር ልማት በትኩረት እየተሠራ ነው ብለዋል። ባሕርዳር፣ ጎንደር፣ ደሴ እና ኮምቦልቻ የመጀመሪያ ምዕራፍ አጠናቅቀው ወደ ሁለተኛ ምዕራፍ ተሸጋግረዋል ነው ያሉት።
የኮሪደር ልማት ለዘመናት ሰው እንዳያያቸው አድርገን በጉያችን የደበቅናቸውን የቱሪዝም መስህቦችን እና የኢንቨስትመንት አቅሞችን የገለጠ፣ ባሕርዳርን ከጣና ሐይቅ ጋር ያስተሳሰረ፣ ጎንደርን እንደገና የሞሸረ፣ በእርጅና የቆየችውን ደሴን ዳግም ያስዋበ ለኮምቦልቻ እና ለደብረ ብርሃን ከኢንዱስትሪ ከተማነታቸው ባሻገር የቱሪዝም ስጦታ ያበረከተ ነው ብለዋል።
የኮሪደር ልማት የስማርት ሲቲ ትግበራ አንዱ አካል ተደርጎ እየተሠራ መኾኑን ነው የተናገሩት። የኮሪደር ልማት ለዜጎች ደኅንነት ትልቅ አስተዋጽኦ እያደረገ መኾኑንም ገልጸዋል።
የኮሪደር ልማት ተቀዛቅዞ የቆዬውን ኮንስትራክሽን ያነቃቃ፣ ፕሮጄክቶችን በጥራት እና በፍጥነት የማጠናቀቅ ልምድ የተገኘበት ነው ብለዋል።
ለዜጎች የሥራ ዕድል በመፍጠርም ትልቅ አስተዋጽኦ እያደረገ መኾኑን ነው ያብራሩት። የኮሪደር ልማት የሕዝብ እና የመንግሥትን አንድነት ያረጋገጠ፣ የሀገር ወዳድነትን ስሜት በተግባር ያሳየ እንደኾነም አስገንዝበዋል።
በክልሉ ዲጂታላይዜሽንን ለማስፋፋት በትኩረት መሠራቱንም ተናግረዋል። የኀይል አቅርቦት እና ተደራሽነትን ለማሳደግ እንደተሠራም ገልጸዋል።
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን