
ባሕር ዳር፡ ግንቦት 28/2012 ዓ.ም (አብመድ) በክልሉ የአረንጓዴ አሻራ ችግኝ ተከላ መርሃ ግብር በ” ደከር ” አካባቢ ዛሬ ተጀምሯል።
ርዕሰ መስተዳድሩ መርሃ ግብሩን ሲያስጀምሩ እንደገለጹት በክልሉ ባለፈው ዓመት የአረንጓዴ አሻራ ቀን ከተተከለው ከ190 ሺህ በላይ ችግኝ ውስጥ 80 በመቶው ጸድቋል። በክልሉ በዚህ የክረምት ወቅትም የኮሮና ቫይረስን ከመከላከሉ በተጓዳኝ የችግኝ ተከላ መርሃ ግብሩ ይካሄዳል። የክልሉ መንግስት የጀመራቸው የአረንጓዴ ልማት ሥራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉም አቶ ኦርዲን አስታውቀዋል።
ችግኞችን በመትከል እና በመንከባከብ አረንጓዴ አካባቢን ለመፍጠር በሚካሄደው እንቅስቃሴ ወጣቶች፣ ተማሪዎች እና አርሶ አደሮችን ጨምሮ መላው የክልሉ ኅብረተሰብ ርብርብ እንዲያደርጉም ጥሪ አቅርበዋል።
የክልሉ የግብርና ቢሮ ኃላፊ አቶ ወርዲ ሐሺም ደግሞ “ችግኝ መትከል ብቻ ሳይሆን እንዴት መጽደቅ እንዳለበት እቅድ አውጥተን እየሠራን እንገኛለን” ብለዋል፡፡
በዘንድሮ የአረንጓዴ ልማት ሥራ በክልሉ ከ2 ሚሊዮን 500 ሺህ በላይ ችግኞችን ለመትከል እንደታቀደም ገልጸዋል ሲል ኢዜአ ዘግቧል፡፡
በክልሉ በዛሬው የአረንጓዴ አሻራ ቀን የችግኝ ተከላ መርሃ ግብር ርዕሰ መስተዳድሩን ጨምሮ ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች፣ የኃይማኖት አባቶች፣ ወጣቶች እና ሌሎችም የኅብረተሰብ ክፍሎች ተሳትፈዋል።