“ለእናቶች ቀድመን መድረስ ያለብን ሴቶች ነን”

28

ባሕር ዳር: ሐምሌ 18/2017 ዓ.ም (አሚኮ) ‎የአማራ ሴቶች ማኅበራት ፌዴሬሽን የቦርድ መሪዎች፣ አባል ማኅበራት እና ተጋባዥ እንግዶች በተገኙበት የችግኝ ተከላ እና የደም ልገሳ መርሐ ግብር ተካሂደዋል።

‎የችግኝ ተከላው በባሕር ዳር ከተማ ለፌዴሬሽኑ ሕንፃ መገንቢያ በተሰጠው ቦታ ላይ ነው የተካሄደው።

በ‎መርሐ ግብሩ ለተሳታፊዎች ከባሕር ዳር ደም ባንክ አገልግሎት በባለሙያዎች የደም ልገሳን አስፈላጊነት እና ጥቅሞች ገለፃ ከተደረገ በኋላ ተሳታፊዎች ደም ለግሰዋል።

‎ደም የለገሱት የፌዴሬሽኑ ምክትል ቦርድ ሠብሣቢ እና የአማራ ክልል ሴቶች፣ ሕጻናት እና ማኅበራዊ ጉዳይ ቢሮ ምክትል ኀላፊ ንፁህ ሽፈራው ደም ሲለግሱ የአሁኑ ለአምስተኛ ጊዜ መኾኑን ተናግረዋል።

“‎‎ደም የሚፈልጉ በርካታ እናቶች ስላሉ ለእነሱ ደም በመስጠቴ ደስተኛ ነኝ” ብለዋል።

‎”ለእናቶች ቀድመን መድረስ ያለብን ሴቶች ነን” ያሉት ወይዘሮ ንፁህ ሽፈራው ሁሉም የሚችል ሰው ደም ሊለግስ ይገባል ነው ያሉት።

‎ሌላው ደም ለጋሽ የፌዴሬሽኑ የፋይናንስ ባለሙያ ዐቢይ ወርቁ ”የኔ ደም የሰው ሕይወት የሚያተርፍ ከኾነ መስጠት አያጎድልምና ሁሌም እለግሳለሁ” ብለዋል።

‎ደም ሲለግሱ ይህ ለሦስተኛ ጊዜ ሲኾን ከስጦታዎች ሁሉ ደም መስጠት የሰውን ሕይወት የሚታደግ በመኾኑ ሁሉም ሰው ደም ሊለግስ እንደሚገባ ገልጸዋል።

‎ዘጋቢ:- ፍሬሕይወት አዘዘው

የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
👇👇👇
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation

ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!

Previous articleአካል ጉዳተኞችን ያላካተተ ልማት ውጤታማ መኾን አይችልም።
Next articleየአማራ ክልል ምክር ቤት መደበኛ ጉባኤ ነገ ይጀምራል።