የሃይማኖት አባቶች እና የሀገር ሽማግሌዎች ለተገኘው አንጻራዊ ሰላም ጉልህ ሚና ተጫውተዋል።

20

ጎንደር፡ ሐምሌ 07/2017 ዓ.ም (አሚኮ) ‎‎‎በማዕከላዊ ጎንደር ዞን “ጥንካሬዎቻችን በማስቀጠል እና ጉድለቶቻችንን በማረም ወደ ሁለንተናዊ ስኬት እናመራለን” በሚል መሪ መልዕክት ከሃይማኖት አባቶች እና ከሀገር ሽማግሌዎች ጋር ውይይት ተካሂዷል።

‎በመድረኩ የተገኙት የአማራ ክልል ግብርና ቢሮ አማካሪ ግዛት አብዩ በክልሉ አንጻራዊ ሰላም መፈጠሩን ገልጸዋል። ተፈጥሮ በቆየው የጸጥታ ችግር ምክንያት
ከማኅበረሰቡ ባሕል እና እሴት የወጡ ኢ ሰብአዊ ድርጊቶች መፈጸማቸውን አንስተዋል። ይህንንም ማውገዝ እና ዘላቂ ሰላም ለማረጋገጥ የድርሻን መወጣት ይገባል ብለዋል።

‎መድረኩ የሃይማኖት አባቶች ለሀገር ሰላም የነበራቸውን ተሳትፎ አጠናክረው እንዲቀጥሉ እና ሁሉም ዜጋ የድርሻውን እንዲወጣ ማድረግን ዓላማ ያደረገ መኾኑን ተናግረዋል።

‎የማዕከላዊ ጎንደር ዞን ዋና አሥተዳዳሪ አወቀ አስፈሬ ሰላም እንዲሰፍን ውይይት ቀዳሚው መፍትሔ መኾኑንም አስገንዝበዋል።

‎በዞኑ አንጻራዊ ሰላም መኖሩን ያነሱት አሥተዳዳሪው
አንዳንድ አካባቢዎች ላይ ያሉ ችግሮችን መፍታት እንደሚገባም አመላክተዋል።

‎የሃይማኖት አባቶች እና የሀገር ሽማግሌዎች ለተገኘው አንጻራዊ ሰላም የነበራቸው ሚና ከፍተኛ መኾኑን ተናግረዋል። ላደረጉት አስተዋጽኦ ምሥጋና አቅርበዋል።

‎ችግሮቹን በሰላማዊ መንገድ ለመፍታት የሚያደርጉትን ጥረት በመደገፍ እሴትን መጠበቅ ይገባልም ብለዋል።

‎የጸጥታ ችግሩ ኢኮኖሚያዊ፣ ፖለቲካዊ እና ማኅበራዊ ችግሮች እያስከተለ መኾኑም ተገልጿል።

‎በመድረኩ የተሳተፉ የሃይማኖት አባቶች እና የሀገር ሽማግሌዎች በዞኑ የጸጥታውን ችግር ተከትሎ የተከሰቱ ችግሮች መኖራቸውን አንስተዋል። የጸጥታ ችግሩ መፍትሔ እንዲያገኝም የበኩላቸውን እያበረከቱ መኾኑን ተናግረዋል።

‎መንግሥትም ለሰላም ትኩረት ሰጥቶ እንዲሠራ ጠይቀዋል። ዘላቂ ሰላም እንዲረጋገጥ በጋራ መሥራት እንደሚገባም ተናግረዋል።

‎ታጥቀው የወጡ አካላት የመንግሥትን የሰላም ጥሪ እንዲቀበሉ ለማድረግ ረገድ እየሠሩ መኾናቸውን ተገልጿል።

‎በዞኑ በጸጥታ ችግሩ ምክንያት ከ600ሺህ በላይ ተማሪዎች ከትምህርት ገበታ ውጭ መኾናቸው ተነስቷል። በመሠረተ ልማቶች፣ በጤና ተቋማት እና በሌሎችም አገልግሎቶች ላይ አሉታዊ ተጽዕኖ ማስከተሉም ተመላክቷል።

ዘጋቢ፦ ‎ቃልኪዳን ኃይሌ

የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!

https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation

ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን

Previous articleዛሬ የለገስነው ደም ነገ ለእኛም ነው።
Next articleአልማ በማኅበራዊ ልማት ዘርፎች ያከናወናቸውን ተግባራት የሚያሳይ የፎቶ ኤግዚቪሽን ለዕይታ አቀረበ፡፡