
ደብረ ታቦር: ሐምሌ 05/2017 ዓ.ም (አሚኮ) የደብረ ታቦር ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ በተለያዩ የሙያ መስኮች ያሠለጠናቸውን 315 ተማሪዎችን ለ28ኛ ጊዜ አስመርቋል። ከተመራቂዎች ውስጥ 173 የሚኾኑት ሴት ናቸው።
በምረቃ ሥነ ስርዓቱ መልዕክት ያስተላለፉት የኮሌጁ ዲን በላይ ሙጨ “ሰላም የመልካም ሃሳብ እና ብቁ አዕምሮ ውጤት ነው” ብለዋል። የአንድን ሀገር ሰላም፣ ልማት እና ዕድገት ለማፋጠን እና የኅብረተሰብን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ቁልፉ እና የማይተካው የሰው ሃብት በመኾኑ በትኩረት መሥራት ይገባል ብለዋል።
ኮሌጁ ከተቋቋመበት ጊዜ ጀምሮ በተለያዩ የሥልጠና ሙያዎች እና ደረጃዎች በርካታ የሰው ኃይል በማስመረቅ ወደ ገበያው ማሰማራቱን አቶ በላይ ተናግረዋል።
የደብረ ታቦር ከተማ አሥተዳደር ምክትል ከንቲባ ኃይለኢየሱስ ሰለሞን የአንድን ሀገር ልማት ለማፋጠን ትልቁ ቁልፍ የሰው ኃይል እንደኾነ ተናግረዋል። የደብረ ታቦር ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅም በተለያዩ የሙያ መስኮች በማሠልጠን ትኩረት ሰጥቶ እየሠራ ያለ ተቋም መኾኑን አንስተዋል።
ተመራቂ ተማሪዎች ከአንደኛው ወደ ሌላኛው ምዕራፍ ሽግግር የሚያደርጉበት ዕለት መኾኑን ተናግረዋል። ተመራቂዎች ከሥልጠና ወደ ሙያ በሚገቡበት ወቅት ሁሉም ከጎናቸው በመኾን ማበረታታት እንዳለበት አሳስበዋል።
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
👇👇👇
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን