ኢትዮጵያ እና ሱዳን የሦስትዮሽ ድርድሩን ለማስጀመር ተስማሙ፡፡

289

ባሕር ዳር፡ ግንቦት 26/2012 ዓ.ም (አብመድ) ኢትዮጵያ እና ሱዳን የታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ የሦስትዮሽ ድርድርን ለማስቀጠል መስማማታቸውን የውኃ፣ መስኖና ኢነርጂ ሚኒስቴር አስታውቋል፡፡

ሚኒስትሩ ስለሽ በቀለ (ዶክተር ኢንጂነር) እና ልዑካቸው ዛሬ ከሱዳን አቻቸው ፕሮፌሰር ያሲር አባስ ሞሐመድ እና ልዑካቸው ጋር በቪዲዮ ኮንፈረንስ ተወያይተዋል፡፡

የሁለቱ ሀገራት ልዑካን የታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብን የሦስትዮሽ ድርድር ማስቀጠል በሚቻልባቸው ሀሳቦች ላይ ነው የተወያዩት፡፡

ልዑካኑ የሦስትዮሽ ድርድሩ እንደገና ስለሚጀምርበት፤ ድርድሩ ስለሚከናወንባቸው የስነ ስርዓት ጉዳዮች እና በግድቡ ላይ የሀገራቱ ዋና ዋና ጉዳዮችን በተመለከተ መምከራቸው ተገልጧል፡፡

በውይይታቸውም ሁለቱ ወገኖች የሁለትዮሽ ስብሰባዎችን በአጭር ጊዜ በማጠናቀቅ የሦስትዮሽ ስብሰባው በቶሎ እንዲጀመር ለማመቻቸት መስማማታቸው ታውቋል፡፡

ሁለቱ ወገኖች ከድርድሩ ጋር የተያያዙ ያልተፈቱ ዋና ዋና ጉዳዮችን በተመለከተም እንደተወያዩ የውኃ፣ መስኖና ኢነርጂ ሚኒስቴር አስታውቋል፡፡

Previous articleተጨማሪ 87 ሰዎች በኮሮና ቫይረስ መያዛቸውንና ሁለት ሰዎች መሞታቸውን ጤና ሚኒስቴር አስታወቀ፡፡
Next article የባሕር ዳር ጭስ ዓባይ መንገድ ሥራን የሚያስቆም የወሰን ማስከበር ችግር አለመኖሩን የባሕር ዳር ዙሪያ ወረዳ አስታውቋል፡፡