
አዲስ አበባ: ሰኔ 27/2017 ዓ.ም (አሚኮ) የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት የኃይል መቆራረጡን ለመቀነስ የክረምት ዝግጅት ላይ ትኩረት አድርጎ እየሠራ መኾኑን አስታውቋል።
የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት የኮሙዩኒኬሽን ሥራ አስፈጻሚ አንዋር አብራር የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት በተደጋገሚ የሚስተዋለውን የኀይል መቆራረጥ በመቀነስ ወደ ዜሮ ለማምጣት በጥናት ላይ የተሞረከዘ የኀይል መቆራረጥ መንስኤዎችን በመለየት ወደ ሥራ መገባቱን ተናግረዋል።
በተደረገው ጥናትም ለኀይል መቆራረጥ ዋና ዋና ምክንያቶች 47 በመቶ የሚሆነውን የሚሸፍነው የዛፎች ንክኪ መኾኑን አንስተዋል። በኤሌክትሪክ መሠረተ ልማት ውስጥ ንክኪ የነበራቸውን ዛፎች በሀገር ደረጃ ቆረጣ ማካሄዳቸውን ገልጸዋል።
ዛፎች በመቆረጣቸው በየዓመቱ ሊከሰት የሚችለውን የኃይል መቆራረጥ ድግግሞሽን በአዲስ አበባ ከተማ 14 ነጥብ 8 በመቶ መቀነስ መቻሉን ተናግረዋል።ለኤሌክትሪክ መሠረተ ልማት ሲባል የተቆረጡ ዛፎችን ለመተካት በክረምቱ የአረንጓዴ አሻራ መርሐ ግብር እንደ ተቋም በሀገር ደረጃ 100ሺህ ችግኞችን ለመትከል ዝግጅት መጠናቀቁን አመላክተዋል።
በሀገር አቀፍ ደረጃ የኀይል መቆራረጥን ወደ ዜሮ ለማምጣት፣ በዝናብ ምክንያት የሚመጡ አደጋን ለመቀነስ እና ለመቆጣጠር በ100 ቀናት እቅድ ዝግጅት ተደርጓል ብለዋል።
ዘጋቢ:- ራሄል ደምሰው
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
👇👇👇
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!