
ደብረ ብርሃን: ግንቦት 19/2017 ዓ.ም (አሚኮ) በደብረ ብርሃን ከተማ አሥተዳደር የሚገኙ የጤና ባለሙያዎች ከከተማ አሥተዳደሩ የሥራ ኀላፊዎች ጋር በወቅታዊ ጉዳዮች ዙሪያ ውይይት አድርገዋል።
የጤናው ዘርፍ አርበኝነት ለሀገር ግንባታ ያለውን ፋይዳ በመረዳት የዘርፉ ባለሙያዎች እና መሪዎች ሚናቸውን በአግባቡ ሊወጡ እንደሚገባ የደብረ ብርሃን ከተማ አሥተዳደር ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ በድሉ ውብሸት አሳስበዋል፡፡
የውይይቱ ተሳታፊዎች የተለያዩ ጥያቄዎችን አንስተው ምላሾች ተሰጥቶባቸዋል። ባለሙያዎቹ ያነሷቸውን ጥያቄዎች በአግባቡ በመያዝ አሥተዳደሩ የሚፈታቸውን ለይቶ ምላሽ ለመስጠት ይሠራል ብለዋል ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባው።
ከመኖሪያ ቤት አቅርቦት አኳያ ባለሙያዎች የቤት ባለቤት መኾን የሚችሉበት አግባብ ላይ አሥተዳደሩ ትኩረት አድርጎ ይሠራልም ብለዋል።
በውይይቱ የተሳተፉ የጤና ባለሙያዎች ከደመወዝ እና ጥቅማ ጥቅም፣ የሥራ ቦታ ደኅንነት፣ የሥራ ቦታ ምቹነት እና ሌሎች ጥያቄዎችን አንስተዋል።
የደብረ ብርሃን ከተማ አሥተዳደር ጤና መምሪያ ኀላፊ በቀለ ገብሬ የጤና ባለሙያዎች እንደ ሀገር ለመጣው ለውጥ የነበራቸው አበርክቶ ትልቅ ስፍራ የሚሰጠው መኾኑን ጠቅሰዋል፡፡
ጤናማ እና አምራች ማኅበረሰብ ለመፍጠር የባለሙያዎች ሚና ትልቁን ድርሻ ይወስዳል ነው ያሉት ኀላፊው። ዘርፉን ለመለወጥ መሠረታዊ የማሻሻያ ሥራዎችን በማከናወን የሚነሱ ጥያቄዎች በሂደቱ ምላሽ ማግኘት የሚችሉበት አግባብ ይፈጠራል ብለዋል።
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
👇👇👇
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን