
አዲስ አበባ: ግንቦት 14/2017 ዓ.ም (አሚኮ) ሦስተኛው የቀይ ባሕር እና የባሕረሰላጤው አካባቢ ውይይት በአዲስ አበባ እየተካሔደ ነው። ውይይቱ “የባሕረሰላጤው እና የአፍሪካ ቀንድ ሀገራት ትብብርን ማሰስ” የሚል መሪ መልዕክት አለው። ኢትዮጵያ የባሕር በር የሌላት ሀገር ብትኾንም በቀጣናው የውኃ ደኅንነት እና ኹኔታ ላይ ሀሳብ የማንሳት ሙሉ መብት አላት ብለዋል የውጭ ጉዳይ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ጃፋር በድሩ።
የቀይ ባሕር እና የባሕረ ሰላጤው አካባቢ የኢኮኖሚ እና የደኅንነት ጉዳይ ብሎም የፖለቲካ መጫዎቻ መድረክ ነውም ብለዋል። አቶ ጃፋር ከዚህ በፊት እንደነበረው ኢትዮጵያ የዚህ ኮሪደር ተሳትፎ ላይ በተመልካችነት የምትቆም ሳይኾን በአግባቡ የሚገባትን ለማግኘት የምትሔድበት ጊዜ ነው ብለዋል።
የውጭ ጉዳይ ኢንስቲትዩት ባዘጋጀው በዚህ መድረክ ከሶማሊያ፣ ከሳዑዲ አረቢያ፣ ከእስራኤል፣ ከሱማሌ ላንድ ፣ ከተባበሩት አረብ ኤምሬቶች፣ ከኢትዮጵያ እና ከሌሎች ሀገራት የተውጣጡ ፖሊሲ አውጭ ምሁራን ተገኝተዋል።
ይህ ቀጣናዊ የምክክር መድረክ የሰላጤው እና የአፍሪካ ቀንድ የንግድ እና ኢንቨስትመንት ኹኔታ ላይ እንዲኹም ያላቸው የመልማት ዕድሎች፣ የጂኦ ፖለቲካ ኹኔታ፣ የኢኖኖሚ እና ደኅንነት ላይ አተኩሮ እየመከረ ለሁለት ቀናት ይቆያል።
ዘጋቢ፦ አንዱዓለም መናን
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
👇👇👇
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን