
እንጅባራ: ግንቦት 06/2017 ዓ.ም (አሚኮ) በአዊ ብሔረሰብ አሥተዳደር ከመንግሥት ሠራተኞች ጋር በወቅታዊ የሰላም እና የጸጥታ ጉዳዮች ዙሪያ ውይይት ተካሂዷል። ውይይቱ በክልሉ በተፈጠረው ግጭት የደረሰው ጉዳት እና ከችግሩ መውጫ መንገዶች ላይ ያተኮረ ነው።
የአዊ ብሔረሰብ አሥተዳደር ዋና አሥተዳዳሪ ቴዎድሮስ እንዳለው የተፈጠረው ግጭት በክልሉ ሕዝብ ላይ መጠነ ሰፊ ጉዳት ማድረሱን ተናግረዋል። የጽንፈኝነት አስተሳሰቦች እና ተግባራትን በጋራ መታገል እንደሚገባም አስገንዝበዋል። ሰላም ከማንም የማንጠብቀው፣ በእጃችን ያለ እና በሁላችን የጋራ ጥረት የሚጸና ሃብት ነው ብለዋል።
የመንግሥት ሠራተኞች የአገልግሎት አሰጣጥ ጥራትን በማሻሻል ለዘላቂ ሰላም መረጋገጥ ያላቸውን ሚና በአግባቡ ሊወጡ እንደሚገባም ገልጸዋል። የአማራ ሚዲያ ኮርፖሬሽን የዋና ሥራ አስፈጻሚው አማካሪ ግዛቸው ሙሉነህ በክልሉ የተፈጠረው ግጭት ኅብረተሰቡ ለዘመናት ለፍቶ ያፈራቸውን አንጡራ ሀብቶች እያወደመ መኾኑን ተናግረዋል።
የተፈጠረው ቀውስ መቋጫውን እንዲያገኝ የመንግሥት ሠራተኞች ድርብ ኀላፊነት እንዳለባቸውም አስገንዝበዋል። የውይይቱ ተሳታፊዎችም በክልሉ እየተፈጠረ ያለው ግጭት ከግጭት ለመጠቀም ከሚደረግ የተሳሳተ አስተሳሰብ የሚመነጭ ነው ብለዋል። ማኅበራዊ እና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴዎችን የሚገድብ የትግል አካሄድ ሀገርን ለድህነት እና ተረጅነት የሚዳርግ ነው ያሉት ተሳታፊዎቹ የሰላም አማራጮችን መከተል መተኪያ የሌለው ጉዳይ እንደኾነም ገልጸዋል።
ዘጋቢ: ሳሙኤል አማረ
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን