“ቀድሞ የበቀለን ጆሮ በኋላ የመጣ ቀንድ ሊቀድመው ይችላል” ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ.ር)

62

ባሕር ዳር: ግንቦት 01/2017 ዓ.ም (አሚኮ) ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ.ር) የወንጅ ስኳር ፋብሪካን አስመልክተው በማኅበራዊ ትስስር ገጻቸው መልእክት አስተላልፈዋል። ሪፎርም እንዴት እንደሚሠራ ቋሚ ዐውደ ርዕይ የሚኾን ውጤት በወንጂ ሸዋ ስኳር ፋብሪካ ተመለከትን። የወንጂ ስኳር ፋብሪካ የዛሬ 70 ዓመት ነበር በጥሩ መሠረት ላይ የተገነባው።

ከዘመን ጋር ካልተጓዙ መቅደም ብቻውን መብለጥን አያመጣም። “ቀድሞ የበቀለን ጆሮ በኋላ የመጣ ቀንድ ሊቀድመው ይችላል” ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ እየፈጠኑ እና እየፈጠሩ ዘመኑን ካልቀደሙት፣ ጊዜው ራሱ ይቀድማል። ወንጂ ስኳር ፋብሪካ የዛሬ ሦስት ዓመት ለሠራተኞቹ ደሞዝ መክፈል ተስኖት ነበር። ዕዳ እንደ መርግ ተጭኖት ነበር። በተሠራው የሪፎርም ሥራ፣ ዛሬ ከ1500 ኩንታል የቀን ምርት ወደ 7000 ኩንታል በቀን ለማደግ ችሏል። ከዚህም ባሻገር ለ14 ዓመታት ከሥራ ውጭ የነበረው የብዙዎች ትዝታ፣ ደስታ ከረሜላ እንደገና መመረት ጀምሯል።

በሌማት ትሩፋት በቀን 3000 ሊትር ወትት እና 20 ሺ ዕንቁላል ማምረት የሚችል ሥራ ተሠርቷል። ግቢው እና መስኩ ለዓይን ይማርካል። ወንጂ ዘንድሮ የፈተናውን ዘመን አልፎ፣ በዘጠኝ ወር ውስጥ 8 ነጥብ 7 ቢልየን ብር ገቢ አስገብቷል። ይሄ ጠንካራ የሪፎርም ውጤት በሌሎቹ ፋብሪካዎች እንደሚደገም ይጠበቃል። ከሠራን ነገን እንቀድመዋለን።

የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
👇👇👇
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation

ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!

Previous articleኅብረተሰቡ ጽንፈኝነትን በጽናት ሊያወግዘው እንደሚገባ ተገለጸ።
Next articleበክልሉ ዘላቂ ሰላም እንዲሰፍን የመንግሥት ሠራተኞች ሚና ከፍተኛ መኾን አለበት።