
አዲስ አበባ: ሚያዝያ 29/2017 ዓ.ም (አሚኮ) የኢትዮጵያ የኅብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት የኅብረተሰብ ጤና አደጋዎችን ለመከላከል እና ለመቆጣጠር የሚያስችል የብሔራዊ የኅብረተሰብ ጤና አደጋዎች ማስተባበሪያ የልህቀት ማዕከል አቋቁሟል።
የተቋቋመው የልህቀት ማዕከልን በማጠናከር ጎረቤት ሀገራት ተሞክሮን እንዲወስዱ የሚያስችል መድረክ በማዘጋጀትም በጤናው ዘርፍ ከሚሠሩ ተቋማት ጋር በማዕከሉ ዙሪያ ውይይት እና የፕሮግራም ማስጀመሪያ አካሂዷል።
በውይይቱ ላይ መልዕክት ያስተላለፉት የጤና ሚኒስቴር ዴኤታ ዶክተር ደረጀ ድጉማ መንግሥት የሕዝብን ጤና ለመጠበቅ የኅብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩትን በማጠናከር በትኩረት እየሠራን ነው ብለዋል።
የኢትዮጵያ የኅብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት ዋና ዳሬክተር ዶክተር መሳይ ኀይሉ የዛሬው የውይይት አና የልምድ ልውውጥ መድረክ ኢትዮጵያ በሽታን ለመከላከል እየሠራች ያለውን የሥራ ክንውን ለጎረቤት ሀገራት ለማሳየት የተዘጋጀ መኾኑን ገልጸዋል።
በቀጣይ የኅበርተሰብ ጤና አደጋዎች ቁጥጥር ሥርዓቱን በማጠናከርና በማዘመን ተቋሙ በሰፊው እንደሚሠራ ገልጸዋል።
ዘጋቢ:- ራሄል ደምሰው
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
👇👇👇
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን