
አዲስ አበባ:ሚያዝያ 14/2017 ዓ.ም (አሚኮ) በጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት አስተባባሪነት የፌዴራል ተቋማት እና የብልጽግና ፓርቲ ጽሕፈት ቤት ከፍተኛ መሪዎች በከተማዋ እየተከናወኑ ያሉ የተለያዩ የልማት ሥራዎችን ጎብኝተዋል።
ጉብኝቱ በከተማዋ የተከናወኑ እና በመከናወን ላይ የሚገኙ የኮሪደር ልማት ሥራዎችን፣ የመልሶ ማልማት እና የወንዝ ዳርቻ ፕሮጀክቶችን ጨምሮ ሌሎች በርካታ የልማት ሥራዎችን ያካተተ ነው።
የፌዴራል ተቋማት የሥራ መሪዎች በአዲስ አበባ ከተማ እየተገነቡ ያሉ የልማት ሥራዎች ሰው ተኮር በመኾናቸው የኅብረተሰቡን ችግር የሚያቃልሉ እና የከተማዋን ዕድገት የሚያፋጥኑ መኾናቸውን ተናግረዋል።
በመዲናዋ እየተከናወኑ የሚገኙት የልማት ሥራዎች ለነዋሪዎች ምቹ የኾነ አካባቢን የሚፈጥሩ ከመኾኑም በላይ የከተማዋን ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነት ያሳድጋሉ ነው ያሉት።
እነዚህ የልማት ሥራዎች የነዋሪዎችን ምቾት በጠበቀ መልኩ እየተከናወኑ መኾኑን የተናገሩት ጎብኝዎቹ ሥራውንም አድንቀዋል።
የከተማዋ የልማት ሥራዎች አዲስ አበባ በሁሉም ዘርፍ የተሟላች ዘመናዊ ከተማ እንድትኾን የሚያስችሉ እንደኾኑም ተገልጿል።
ዘጋቢ፦ሰለሞን አሰፌ
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን