
አዲስ አበባ: መጋቢት 27/2017 ዓ.ም (አሚኮ) የሹዋሊድ በዓል ሹሉምአህመድ እና አውአቅብራ በሚባሉ ቦታዎች እየተከበረ ነው።
የሹዋሊድ በዓል በተባበሩት መንግሥታት የትምህርት፣ የሳይንስ እና የባሕል ድርጅት (ዩኔስኮ) ከተመዘገቡ የማይዳሰሱ ቅርሶች ሁለተኛው ነው።
በዓሉ በሐረሪ ክልል የሮመዳን ጾም በተፈታ ስድስተኛው ቀን በየዓመቱ ይከበራል።
ከክልሉ ነዋሪዎች በተጨማሪ በበዓሉ ላይ ለመታደም ከአፋር፣ ሱማሌ፣ ኦሮሚያ እና ሌሎች አጎራባች ክልሎች በርካታ ዜጎች መገኘታቸውንም የሐረሪ ክልል ባሕል፣ ቅርስ እና ቱሪዝም ቢሮ ኀላፊ ተወለዳ አብዶሽ ለአሚኮ ገልጸዋል።
በዓሉን ለማክበር የውጭ ሀገር ቱሪስቶች መገኘታቸውንም ኀላፊው ጠቁመዋል።
የሹዋሊድ በዓል የሕዝቦችን አብሮነት ወንድማማችነት እና መቀራረብን ለማጠናከር ከሚያስችሉ ታታላቅ ባሕላዊ በዓላት መካከል አንዱ እና ዋነኛው ነው ብለዋል።
በበዓሉ ልጃገረዶች፣ ወጣቶች፣ እናቶች፣ የሀገር ሽማግሌዎች፣ የሃይማኖት አባቶች በተለያዩ ሃይማኖታዊ ይዘት ባላቸው ባሕላዊ ክዋኔዎች እንደሚያከብሩት ነው አቶ ተወለዳ የነገሩን።
በበዓሉ ስለ ሰላም የሚሰብኩ ሃይማኖታዊ መወድሶች እንደሚቀርቡም ተጠቁሟል።
ዘጋቢ፦ ቴዎድሮስ ደሴ- ከሐረር
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
👇👇👇
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!