
ደብረማርቆስ፡ መጋቢት 21/2017 ዓ.ም (አሚኮ) 1ሺህ 446ኛው የዒድ አል ፈጥር በዓል በደብረ ማርቆስ ከተማ በሃይማኖታዊ ሥርዓት ተከብሯል።
የረመዳን ወር በእስልምና ሃይማኖት ቅዱስ እና ታላቅ ወር ነው።
የሙስሊሙ ማኅበረሰብ ይሄን ታላቅ ወር በጾም፣ በሶላት እና አቅም ያጡትን በመርዳት ያሳልፋል። የረመዳን ጾም የመጨረሻ ቀን የዒድ አልፈጥር በዓል በታላቅ ሃይማኖታዊ ሥነ ሥርዓት ይከበራል።
በደብረ ማርቆስ ከተማ አሥተዳደርም 1ሺህ 446ኛው የዒድ አል ፈጥር በዓል በሃይማኖታዊ ሥነ ሥርዓት ተከብሯል።
በበዓሉ ላይ ተገኝተው መልዕክት ያስተላለፉት የምሥራቅ ጎጃም ዞን ሸሪዓ ፍርድ ቤት ሠብሣቢ ሼህ ወለላው ሰይድ የሙስሊሙ ማኅበረሰብ በረመዳን ወቅት በዱዓ እና በሶላት ለሀገር በመጸለይ ሲያሳልፍ እንደቆየ ተናግረዋል።
የዒድ አልፈጥር በዓልን ሲያከበርም በመረዳዳት እና በመተጋገዝ ሃይማኖቱ በሚያዘው መሠረት በጎ ተግባር በመሥራት ሊኾን ይገባል ብለዋል። አቅም ያጡትን በማሰብ መርዳት እና መደገፍ የሃይማኖቱ ግዴታ መኾኑንም ጠቅሰዋል።
ሰላም ለሁሉም ነገር አስፈላጊ በመኾኑ በቀጣይም የሙስሊሙ ማኅበረሰብ ስለ ሰላም ዱዓ ከማድረግ ባለፈ ሰላም እንዲሰፍን የበኩሉን ድርሻ ማበርከት ይገባዋልም ብለዋል።
የሃይማኖቱ ተከታዮችም ለሀገር የሚጠቅም ሥራ ለመሥራት ሰላም ቀዳሚ በመኾኑ ለሰላም እንደሚተጉም ተናግረዋል።
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
👇👇👇
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!