
ወልድያ: መጋቢት 12/2017 ዓ.ም (አሚኮ) የወልድያ ከተማ አሥተዳደር ሲቪል ሰርቪስና የሰው ሃብት ልማት መምሪያ ከመንግሥት ሠራተኞች ጋር የ2017 በጀት ዓመት የ6 ወር የለውጥ ሥራዎች፣ አገልግሎት አሰጣጥ እና መልካም አሥተዳደር ሥራዎች ግምገማ አካሂዷል።
የወልድያ ከተማ አሥተዳደር ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ ዱባለ አብራሬ ተቋማት የራሳችን እንደኾኑ አስበን የጋራ ሀገራችንን ለመገንባት እና የጋራ ሕልማችንን ከግብ ለማድረስ ልንሠራ ይገባል ብለዋል።
የመንግሥት ሠራተኞች በአገልግሎት አሰጣጥ ላይ የሚታዩ ችግሮችን በመፍታት ኅብረተሰቡ ከምሬት ወጥቶ የሚያመሰግንበት አገልግሎት ለመሥጠት መሥራት ይገባቸዋል ነው ያሉት።
የወልድያ ከተማ አሥተዳደር ሲቪል ሰርቪስና የሰው ሃብት ልማት መምሪያ ኀላፊ አስናቀች ኀይሌ የሪፎርሙን አተገባበር ክትትል እና ድጋፍ በማድረግ የአገልግሎት አሰጣጡን ለማሻሻል እየሠራን ነው ብለዋል።
የደምበኞችን የአገልግሎት ርካታ በመፈተሽ ቅሬታዎችን ለመፍታት ተከታታይ ሥራ እየተሠራ መኾኑን ተናግረዋል።
የውይይቱ ተሳታፊዎች ሪፎርሙን መተግበር ቁልፍ ተግባራትን አቅደን ለመሥራት መንገድ ጠርጎልናል ነው ያሉት። የሚያገለግሉትን ሕዝብ ያለቅሬታ ለማስተናገድ እንደሚያግዛቸውም ተናግረዋል።
ሕዝባቸውን በቅንነት በማገልገል ለከተማዋ ብሎም ለሀገር እድገት ድርሻቸውን እንደሚወጡም ገልጸዋል።
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
👇👇👇
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን