
ባሕር ዳር: መጋቢት 04/2017 ዓ.ም (አሚኮ) ፓሮን ትሬዲንግ የተሰኘው ሀገር በቀል ኩባንያ በባሕር ዳር ልዩ የኢኮኖሚ ዞን በ500 ሚሊዮን ብር ካፒታል በቆሎን በማቀነባበር ስታርች ለማምረት የሚያስችል የማሽን ተከላ ሥራዎችን በማጠናቀቅ የሙከራ ምርት ማምረት መጀመሩን አስታውቋል።
የባሕር ዳር ልዩ የኢኮኖሚ ዞን ዋና ሥራ አሥኪያጅ ጥሩየ ቁሜ ኩባንያው ሁለት ሄክታር መሬት ተረክቦ የግንባታ እና የማሽን ተከላ ሥራዎችን ሲያከናውን ቆይቷል ብለዋል። ኩባንያው ከ4ሺህ በላይ ከሚኾኑ አርሶ አደሮች ጋር ዘላቂ የምርት አቅርቦት እንዲኖር የሚያስችል የገበያ ትስስር መፍጠሩም ተገልጿል።
ፓሮን ትሬዲንግ ምርቱን ለሀገር ውስጥ እና ለውጭ ገበያ ለማቅረብ ፕሮጀክት ፕሮፖዛል ማቅረቡን የገለጹት ሥራ አስኪያጇ ኩባንያው በቆሎን በግብዓትነት እንደሚጠቀም ተናግረዋል። ይህም ለአካባቢው በቆሎ አምራች አርሶ አደሮች ቀጣይነት ያለው የገበያ ትስስር ከመፍጠሩ በተጨማሪ በሥራ ዕድል ፈጠራ ላይ ትልቅ አስተዋጽኦ እንደሚያበረክት ተናግረዋል።
ኩባንያው አሁን ላይ ለ300 የአካባቢው ወጣቶች ዘላቂ የሥራ ዕድል ፈጥሯል። በሙሉ አቅሙ ወደ ሥራ ሲገባ ከ1ሺህ በላይ ዜጎችን ተጠቃሚ እንደሚያደርግ ይጠበቃል። ይህ ኢንቨስትመንት በአካባቢው የኢኮኖሚ ዕድገት ላይ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንደሚያበረክትም ከኢትዮጵያ ኢንዱስትሪ ፓርክ ልማት ኮርፖሬሽን የተገኘው መረጃ ያመለክታል።
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
👇👇👇
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን