
ወልዲያ: የካቲት 25/2017 ዓ.ም (አሚኮ) በወልዲያ ሲካሄድ የሰነበተው የቀበሌ የሥራ ኀላፊዎችን ሥልጠና ተጠናቅቋል። የክልል እና የወልዲያ ከተማ አሥተዳደር ከፍተኛ የሥራ ኀላፊዎች ሥልጠናውን ሲወስዱ ለቆዩ ሠልጣኞች የሥራ አቅጣጫ ሠጥተዋል።
የአማራ ክልል ውኃ እና ኢነርጂ ቢሮ ኀላፊ ማማሩ አያሌው (ዶ.ር) የወልዲያን ከተማ ሰላም ለማጽናት ከከተማ አሥተዳደሩ መሪዎች በላይ ቀዳሚ ድርሻ ያለው የለም ብለዋል። በተለይም የቀበሌ የሥራ ኀላፊዎች የሀገር መሠረቱ ቀበሌ በመኾኑ ለሚመሩት ሕዝብ የብልጽግናን እሳቤ በማስረጽ ሚናቸውን ሊወጡ እንደሚገባ አሳስበዋል።
“የሥልጠናውን ውጤት ታች ወርዶ በተግባር መፈጸም ይገባል” ነው ያሉት። ከተማዋን በልማት ለማበልጸግ፣ የቱሪዝም እና የኢንዱስትሪ መዳረሻ ለማድረግ መሪዎች ሊሠሩ እንደሚገባም ተናግረዋል።
የወልዲያ ከተማ አሥተዳደር ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ ዱባለ አብራሬ ቀበሌዎች ነዋሪዎቻቸውን በማደራጀት ሰላምን የመጠበቅ ሥራቸውን ሊያጠናክሩ አንደሚገባ ገልጸዋል።
የአካባቢ ዘብ በማደራጀት እና ጠንካራ የጸጥታ መዋቅር በመፍጠር ሰላምን ለማጽናት የቀበሌ የሥራ ኀላፊዎች ትኩረት እንዲያደርጉ ነው ያሳሰቡት።
የሕዝባችንን ደኅንነት የመጠበቅ አደራችንን ከመወጣት ጎን ለጎን ደግሞ ሕዝባችን የልማት ተጠቃሚ እንዲኾን በቅንጅት ልንሠራ ይገባል ነው ያሉት።
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
👇👇👇
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!