
የኦጋዴን ብሔራዊ ነፃ አውጭ ግንባር (ONLF) ማዕከላዊ ኮሚቴ እ.ኤ.አ. በ2018 ከኢትዮጵያ መንግሥት ጋር ያደረገው የሰላም ስምምነት አስመልክቶ የተሰጠ መግለጫ ሙሉ ቃል እንደሚከተለው ቀርቧል። በትላንትናው እለት በ23/06/2017 በኦጋዴን ብሔራዊ ነፃ አውጭ ግንባር (ኦብነግ) ስም “የኢትዮጵያ መንግሥት የሰላም ስምምነቱን ጥሷል” በሚል ከናይሮቢ ኬንያ የተሰጠው መግለጫ ከኦብነግ እውቅና ውጪ መሆኑን እየገለፅን፣ መግለጫው እ.ኤ.አ. በ2018 ኦብነግ ከኢትዮጵያ መንግሥት ጋር በአስመራ የገባውን የሰላም ስምምነት የጣሰና ኦብነግን የማይወክል መሆኑን አበክረን እንገልፃለን።
የአስመራው የሰላም ስምምነት ተከትሎ በሶማሌ ክልል የተፈጠረው ሰላምና ልማት ጥሩ ጅምር ላይ መሆናቸውንና የሕዝባችን የልማት፣ የፖለቲካና የኢኮኖሚ ጥያቄዎች መልስ እያገኙ ሳለ፣ ዛሬ በድርጅቱ ስም የወጣው መግለጫ በጅምር ላይ ያለውን ልማት እውቅና መንፈጉ የሚያሳዝን ነው።
በመሆኑም በጉዳዩ ላይ ኦብነግ የሚከተሉትን ሶስት የአቋም መግለጫ ነጥቦችን ማስተላለፍ ይፈልጋል፦
1. በናይሮቢ ከተማ “በኦብነግ ስም የወጣው መግለጫ የድርጅቱን የማዕከላዊ ኮሚቴ አባላት፣ ሥራ አስፈፃሚ እና የኦብነግ ም/ሊቀመንበር አብዱልከሪም ሼህ ሙሴ እውቅና ውጭ በተወሰኑ ግለሰቦች ፍላጎት የወጣ በመሆኑ ድርጅቱን የሚወክል አይደለም።
2. የኦጋዴን ብሔራዊ ነፃ አውጭ ግንባር (ኦብነግ) የአስመራው የሰላም ስምምነት እንደሚደግፍ እና የጀመረውን ሰላማዊ የፖለቲካ ትግል አጠናክሮ በመቀጠል ስምምነቱን በተሻለ መልኩ ተፈፃሚ የምናደርግ ሲሆን፣ እስካሁንም የፌዴራል እና የሶማሌ ክልል መንግሥት ለአስመራው ስምምነት ተግባራዊነት ላደረጉት አስተዋጽኦ እውቅናን እንሰጣለን።
3. የኦጋዴን ብሔራዊ ነፃ አውጭ ግንባር (ኦብነግ) በኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ደንብ አማካኝነት በቅርቡ ጉባኤ የሚናካሄድ ሲሆን፣ በጉባኤው ሰላማዊ ትግሉን የሚያጠናክሩ ውሳኔዎችና አቅጣጫዎችን ያስቀምጣል። በመጨረሻም በኦብነግ ጉዳይ ዙሪያ በተወሰኑ ግለሰቦች የሚሰጡ የተሳሳቱ መግለጫዎች ኅብረተሰቡ እንዳይደናገርና ግለሰቦቹም ከድርጊታቸው እንዲቆጠቡ እናሳስባለን።
ዘላለማዊ ክብር ለሰማዕቶቻችን!!
የኦብነግ ማዕከላዊ ኮሚቴ
ጅግጅጋ
