
ባሕር ዳር: የካቲት 23/2017 ዓ.ም (አሚኮ) የዓድዋ ድል በዓል “ዓድዋ የጥቁር ሕዝቦች ድል” በሚል መሪ መልዕክት በአዲስ አበባ እየተከበረ ነው።
በክብረ በዓሉ ላይ መልዕክት ያስተላለፉት የመከላከያ ሚኒስትሯ ኢንጅነር አይሻ መሐመድ ጀግኖች አባቶች በመስዋዕትነት ያስረከቡንን አደራ በዓድዋ መንፈስ መድገም ይገባል ብለዋል።
ዓድዋ የምንዘክረው ታሪክ ብቻ ሳይኾን ለትውልድ የምናወርሰው ታላቅ ኀላፊነት ነው ያሉት ሚኒስትሯ ዓድዋ የመላው የጥቁር ሕዝቦች የነፃነት በዓል መኾኑን ገልጸዋል።
አፍሪካውያን ለነፃነት የሚያደርጉትን ንቅናቄ በማቀጣጠል ለድል እንዳበቃቸውም ተናግረዋል። ዛሬም በኅብረትና በጀግንነት በመነሳሳት ለሀገራችንና ለአፍሪካ ብልጽግና ለማረጋገጥ መትጋት ይገባል ነው ያሉት።
ጀግኖች አባትና እናቶቻችን በመስዋዕትነት ያስረከቡንን ሀገር አንድነታችንን በማጠናከርና በዘመኑ የገጠሙኑን ፈተናዎችን በመሻገር ጠንካራና የበለጸገች ኢትዮጵያና አፍሪካን ለመገንባት መጠቀም እንደሚገባም ተናግረዋል።
129ኛው የአድዋ ድል ክብረ በዓል በዓድዋ መታሰቢያ ሙዚዬም በተለያዩ ዝግጅቶች እየተከበረ ነው።
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
👇👇👇
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!