ቀበሌዎችን የሰላም እና የልማት ማዕከል ለማድረግ እየሠራ መኾኑን የኦሮሞ ብሔረሰብ አሥተዳደር ገለጸ።

12

ከሚሴ: የካቲት 22/2017 (አሚኮ) በአማራ ክልል ኦሮሞ ብሔረሰብ አሥተዳደር የደዋጨፋ ወረዳ ብልጽግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ”ቀበሌዎቻችንን በማፅናት ሁለንተናዊ እምርታ እናስመዘግባለን” በሚል መሪ መልዕክት በወረዳው ለሚገኙ የቀበሌ አመራሮች ሥልጠና መሰጠት ተጀምሯል።

በማስጀመሪያ መርሐ ግብሩ የኦሮሞ ብሔረሰብ አሥተዳደር ዋና አሥተዳዳሪ አሕመድ አሊ ጠንካራ የሀገረ መንግሥት ግንባታ ሥራችን የሚሳካው በቀበሌዎቻችን ጠንካራ መዋቅር መፍጠር ስንችል ነው በሚል በኹሉም አካባቢ ያለውን የቀበሌ መዋቅር ለማጠናከር ታስቦ የተዘጋጀ ሥልጠና ነው ብለዋል።

የሕዝቦች የልማትና የመልካም አሥተዳደር ጥያቄዎች የሚመለሱት በጠንካራ የቀበሌ መዋቅር በመኾኑ ሠልጣኞች በሥልጠናው ያገኙትን እውቀት በመጠቀም የመፈፀም አቅማቸውን በማጎልበት በቀጣይ ሊሠሩ እንደሚገባ አስረድተዋል።

በቀጣይ የልማት፣ የሰላምና የመልካም አሥተዳደር ሥራዎች የርብርብ ማዕከል ቀበሌ ላይ በማድረግ ለሕዝብ ተጠቃሚነት ለመሥራት ትኩረት ተሰጥቶ እንደሚሠራ ዋና አሥተዳዳሪው ገልጸዋል።

የደዋጨፋ ወረዳ ዋና አሥተዳዳሪ መሐመድ ጌታቸው ተገልጋይና አገልጋይ በቀጥታ የሚገናኙበት መዋቅር ቀበሌ መኾኑን ጠቅሰው ቀበሌ ላይ መሥራት ሀገር ላይ መሥራት ነው በሚል ሥልጠናው እየተሰጠ ነው ብለዋል።
ወረዳው ባሉት ሁሉም ቀበሌዎች ላይ እግር በመትከል የሰላም፣ የልማት እና የመልካም አሥተዳደር ጥያቄዎችን ለመፍታት ጥረት እያደረገ እንደሚገኝም አስገንዝበዋል።

በሥልጠናው የተሳተፉ የቀበሌ አመራሮች በበኩላቸው የክልሉ መንግሥት ቀበሌን የትኩረት ማዕከል በማድረግ ሥልጠና በመስጠቱ መደሰታቸውን ገልጸዋል። በቀጣይ በሥልጠናው በሚያገኙት እውቀት በመጠቀም ለመሥራት መዘጋጀታቸውንም ተናግረዋል።

ዘጋቢ:- ይማም ኢብራሂም

የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
👇👇👇
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation

ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን

Previous article“የዓድዋ ድል በኢትዮጵያዊነት ወኔ የተቀዳጁት የክቡር አክሊል እና ለብሔራዊ ትርክት መሠረት የጣለ የአብሮነት መንፈስ ነው” አፈ ጉባኤ አገኘሁ ተሻገር
Next articleበአማራ ክልል መሪነትን በአግባቡ የሚወጣ የቀበሌ መሪ ለመፍጠር ያለመ ሥልጠና እየተሰጠ ነው።