
ባሕር ዳር: የካቲት 19/2017 ዓ.ም ( አሚኮ) የአማራ ክልል ምክር ቤት የሥራ ኀላፊዎች፣ የክልል ምክር ቤት ጽሕፈት ቤት መሪዎች እና ሠራተኞች በተገኙበት የ2017 በጀት ዓመት የሰባት ወራት ዕቅድ አፈጻጸምን እየገመገመ ነው። የምክር ቤቱ ዋና አፈ ጉባኤ ፍንቱ ተስፋዬ በመክፈቻ ንግግራቸው መድረኩ የተቋሙን አፈጻጸም በመገምገም የነበሩ ጠንካራ ጎኖችን ይበልጥ ለማጎልበት እና ድክመቶችን ለማረም ያለመ መድረክ መኾኑን አንስተዋል።
ተቋሙ የተሰጠውን ሕግ የማውጣት፣ አሥፈጻሚውን እና የዳኝነት አካሉን ክትትል እና ቁጥጥር የማድረግ እና ውክልናን የመወጣት ተግባርን መወጣት ትኩረት ይሰጠዋል ብለዋል። ተልዕኮን በመፈጸም የነበሩትን አፈጻጸሞች በተገቢው በመገንዘብ ውጤታማ አሥተዳደራዊ እና ሙያዊ አገልግሎት በመስጠት በኩል የነበሩትን ጠንካራ አፈጻጸሞች ማጎልበት ይገባል ብለዋል አፈ ጉባኤዋ።
ተቋሙ ለሥራ ኀላፊዎች እና ለምክር ቤት አባላት በአጠቃላይ ለውስጥ እና ለውጭ ደንበኞች የሚሰጠውን አገልግሎት በመዳሰስ በቀሪ ወራት ጉድለቶችን ለይቶ ለማረም የሚያስችል ውይይት ማድረግ ያስፈልጋል ነው ያሉት። በተያዘው በጀት ዓመት ተቋሙ የነበረው የአገልግሎት አሰጣጥ አበረታች መኾኑን አንስተው የሚስተዋሉ ጥቃቅን ጉድለቶችን ማረም ይጠይቃል ብለዋል።
“ትልቁ ሃብት ሰብዓዊ ሃብት ነው” ያሉት አፈ ጉባኤዋ ለተቋሙ ሠራተኞች ምቹ የሥራ አካባቢ የመፍጠር ተግባር ተጠናክሮ ይቀጥላል ማለታቸውን ከክልሉ ምክር ቤት ጽሕፈት ቤት የተገኘው መረጃ ያመለክታል።
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
👇👇👇
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!
