“በበጀት ዓመቱ 111 አምራች ኢንዱስትሪዎች ወደ ምርት ገብተዋል” የአማራ ክልል የኢንዱስትሪ እና ኢንቨስትመንት ቢሮ

49

ባሕር ዳር: የካቲት 13/2017 ዓ.ም (አሚኮ) የአማራ ክልል ኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን የነባር እና አዲስ ፕሮጀክቶች የአፈጻጸም ግምገማ እና የቀጣይ ሥራዎች ዙሪያ ውይይት አድርጓል። የአማራ ክልል ኢንዱስትሪ እና ኢንቨስትመንት ቢሮ ኀላፊ እንድሪስ አብዱ የአማራ ክልል የሀገር ውስጥ እና የውጭ ባለሀብቶች በተለያዩ ኢንቨስትመንቶች ላይ ማሳተፍ የሚያስችል እምቅ ሀብት ባለቤት ነው ብለዋል።

በክልሉ ያለውን ሀብት በተገቢው መንገድ ለመጠቀም ባለፉት ዓመታት በስድስት የልማት ቀጣናዎች ፍኖተ ካርታ በማዘጋጀት የተለያዩ ሥራዎች እየተሠሩ መኾናቸውን አንስተዋል። ከዚህ ውስጥ ደግሞ አንዱ አምራች ኢንዱስትሪዎችን ማስፋት ነው ብለዋል። አምራች ኢንዱስትሪውን ለማበረታታት የክልሉ መንግሥት በክልሉ ዋና ዋና ከተሞች 3 ሺህ 260 ሄክታር መሬት ላይ የኢንዱስትሪ ዞን በመከለል 27 ኢንዱስትሪዎችን ማቋቋም ተችሏል ነው ያሉት።

መሠረተ ልማት ማሟላት እና በዘርፉ የሚታዩ ችግሮችንም መፍታት በመቻሉ አምራች ኢንዱስትሪዎች መነቃቃት አሳይተዋል ብለዋል። ከ2014 አስከ አሁን ከ510 በላይ አነስተኛ፣ መካከለኛ እና ከፍተኛ አምራች ኢንዱስትሪዎች በአዲስ ወደ ምርት መግባታቸውን በማሳያነት አንስተዋል። በ2017 በጀት ዓመት ብቻ 111 አምራች ኢንዱስትሪዎች ወደ ምርት ገብተዋል ነው ያሉት። በዚህም ተኪ እና ወደ ውጭ የሚላኩ ምርቶችን በማምረት እና ከፍተኛ የሥራ ዕድል መፍጠር መቻላቸውን ገልጸዋል።

የኢንዱስትሪዎችን የማምረት አቅም ማሳደግ ላይ ትኩረት ተሰጥቶ ሢሠራ መቆየቱንም አንስተዋል። በ2014 ዓ.ም 49 ነጥብ 4 በመቶ የነበረው የማምረት አቅም አሁን ላይ ወደ 59 ነጥብ 2 በመቶ መድረሱን አንስተዋል። ለውጡ የተገኘው በአምራች ኢንዱስትሪው የሚታዩ ችግሮችን በመቅረፍ መሠረተ ልማት ዝርጋታ ላይ ትኩረት በመሠጠቱ ነው ብለዋል።

በቀጣይ በግንባታ ላይ የሚገኙ መሠረተ ልማቶች በተቀመጠላቸው ጊዜ ተጠናቅቀው የተሟላ አገልግሎት እንዲሠጡ ሁሉም የድርሻውን እንዲወጣ አሳስበዋል።

ዘጋቢ፡- ዳግማዊ ተሠራ

የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!

https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation

ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!

Previous articleየአፈር እና ውኃ እቀባ ሥራው በምርት ገቢያቸው ላይ ጭማሪ እንዳመጣ አርሶ አደሮች ተናገሩ፡፡
Next articleየታክስ እና ጉምሩክ ሥርዓትን ለማዘመን ያለመ የልምድ ልውውጥ ተካሄደ፡፡