
ደሴ: የካቲት 12/2017 ዓ.ም (አሚኮ) በከተማ እና መሠረተ ልማት ሚኒስትር ድኤታ ፋንታ ደጀን የተመራ ልዑክ በደሴ ከተማ አሥተዳደር እየተከናወኑ ያሉ የመሠረተ ልማት ሥራዎችን ተመልክቷል፡፡ የደሴ ከተማ አሥተዳደር የከተማ እና መሠረተ ልማት ዋና ሥራ አሥኪያጅ ቃሲም አበራ ከተማ አሥተዳሩ ከማኅበረሰቡ ጋር በመተባበር እየተከናወኑ ያሉ የመሠረተ ልማት ሥራዎች የከተማዋን ገጽታ በመቀየር ላይ ናቸው ብለዋል፡፡
ከተሞች እያደጉ ሲመጡ ዘመናዊነትን መላበስ ይጠበቅባቸዋል ያሉት አቶ ቃሲም ይህም ተግባር በትኩረት እየተሠራ ነው ብለዋል፡፡ ደሴ ከተማ ልማቷን ስታፋጥን በአካባቢው ካሉ ከተሞች ጋር በቅንጅት እና በትብብር ለመሥራ ጥረት እየተደረገ እንደኾነም ጠቅሰዋል፡፡ ለከተማዋ መሠረተ ልማት ዝርጋታ የክልል እና የፌዴራል ከተማ እና መሠረተ ልማት እያደረጉት ያለው ክትትል እና ድጋፍ አበረታች እንደኾነም ተናረዋል፡፡
የከተማ እና መሠረተ ልማት ሚኒስቴር ሚኒስትር ድኤታ ፋንታ ደጀን በደሴ ከተማ እየተከናወኑ ያሉ የልማት ሥራዎች ለሌሎች አካባቢዎችም ተሞክሮ ሊወሰድባቸው የሚችሉ መኾናቸውን አንስተዋል፡፡ ከተሞች ከሌሎች ከተሞች ልምድ እና ተሞክሮ ከመውሰድ ባለፈ እርስ በእርስ ያላቸውን ትስስር አጠናረው በጋራ ማደግ አለባቸው ነው ያሉት፡፡
ሚኒስትር ድኤታው የከተማ እና መሠረተ ልማት ሚኒስቴር አስፈላጊውን ድጋፍ እና ክትትል እንደሚያደርግ ነው የጠቀሱት፡፡ በደሴ ከተማ የአስፓልት ፕላንት፤ የመናኸሪያ፤ የኮሪደር ልማት እና የስማርት ሲቲ ሥራዎች ላይ ምልከታ የተደረገ ሲኾን ወደፊት መከናዎን ስላለባቸው ሥራዎችም አቅጣጫ ተቀምጧል፡፡
ዘጋቢ:- ደጀን አምባቸው
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!