
ባሕር ዳር: ጥር 25/2017 ዓ.ም (አሚኮ) የቅዱስ መርቆርዮስ ዓመታዊ ክብረ በዓል በደብረ ታቦር እየተከበረ ነው።
ክብረ በዓሉ በሚከበርበት አጅባር ሜዳ የደቡብ ጎንደር ሀገረ ሰብከት ሊቀጳጳስ እና የቅዱስ ሲኖዶስ አባል ብፁዕ አቡነ ሚካኤል፣ የደብረታቦር ከተማ አሥተዳደር ምክትል ከንቲባ ኃይለኢየሱስ ሰሎሞን፣ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፣ እንግዶች እና የሃይማኖቱ ተከታዮች ታድመዋል።
በበዓሉ አባታዊ አስተምህሮ እና መልዕክት ያስተላለፉት የደቡብ ጎንደር ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ እና የቅዱስ ሲኖዶስ አባል ብፁዕ አቡነ ሚካኤል የእግዚአብሔር ክብር ሲገለጽ ምድር ሰላም ትኾናለች ብለዋል። ስለፍቅር፣ ስለአንድነት እና ስለሰላም አብረን ስንቆም መረጋጋት እና መጽናናት ይኾናል ያሉት ብፁዕ አቡነ ሚካኤል ሰላም እና አንድነት እንዲጸና የእኛ መሠባሠብ፣ መመካከር እና መጸለይ ያስፈልጋል ነው ያሉት። ዛሬ በታሪካዊቷ ደብረታቦር ከተማ በዚህ መልኩ መሠባሠባችን ለአብሮነት እና ሰላም ተስፋ ነው ብለዋል።
ብጹዕነታቸው በመልዕክታቸው “በብዙ ፈተና ውስጥ ብናልፍም እግዚአብሔር ከእኛ ጋር ነውና በዓሉን በሰላም ለማክበር ችለናል” ነው ያሉት። በዓሉ በሰላም እንዲከበር ድጋፍ ላደረጉ ሁሉ ብጹዕነታቸው ምሥጋና አቅርበዋል።
ዘጋቢ፦ ታዘብ አራጋው
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!