የቻይና ኮሙኒስት ፓርቲ ማዕከላዊ ኮሚቴ ለብልፅግና ፓርቲ ሁለተኛ ጉባኤ የድጋፍና የመልካም ምኞት መልዕክት ላከ።

39

ባሕር ዳር፡ ጥር 24/2017 ዓ.ም (አሚኮ) ከቻይና ኮሚኒስት ፓርቲ (CPC) ማዕከላዊ ኮሚቴ የተላከው ደብዳቤ በብልፅግና ፓርቲ መሪነት ኢትዮጵያ እያስመዘገበችው ላለው ሁለንተናዊ እድገት ያለውን አድናቆት ገልጿል፤ የሁለትዮሽ ግንኙነቱን ለማጠናከር ቁርጠኛ እንደሆነችም አረጋግጧል።

ብልፅግና ፓርቲ ኢትዮጵያ ተስማሚ የሆነ የእድገትና የዘመናዊነት መንገድ እንድትከተል ከፍተኛ ሚና እየተጫወተ መሆኑን የጠቀሰው መልዕክቱ በሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ ትግበራ የዜጎችን ኑሮን በማሻሻል፣ በአረንጓዴ አሻራ ኢኒሼቲቭ አማካኝነት ዘላቂ የአካባቢ ጥበቃን በማሳደግ፣ የሀገራዊ ምክክር ቅድመ-ዝግጅት በማገባደድ እና ማህበራዊ አንድነትን በማጎልበት ረገድ የተመዘገቡ ውጤቶች በጉልህ እንደሚታዩ ጠቅሷል። እነዚህ ስኬቶች ኢትዮጵያን “የአፍሪካ የብልፅግና ተምሳሌት” እንድትሆን እያስቻለ መሆኑን እውቅና ሰጥቷል፡፡

የቻይና ኮሚኒስት ፓርቲ ማዕከላዊ ኮሚቴው መልዕክት በቀጣይ ዓመታት ፓርቲው ሀገሪቱን ወደ “አዲስና የላቀ ስኬት” መምራቱን እንደሚቀጥል ያለውን እምነት የገለጸ ሲሆን በሁለቱ ሀገራት መካከል ላለው ጥልቅ ትብብር አጽንኦት ሰጥቷል፡፡ የሁለቱ ፓርቲዎች መሪዎች ከዚህ ቀደም የደረሱባቸውን ስምምነቶች ተግባራዊ ማድረግም ጠቃሚ መሆኑ አስምሮበታል።

በቀጣይ የቻይናና የኢትዮጵያ ትብብር በሁሉም ዘርፎች በማስፋትና በማንኛውም ሁኔታ የማይናወጥ ስትራቴጂያዊ አጋርነት ሆኖ የበለጠ እንዲጠናከር ጥሪ አቅርቧል።

ሁለተኛው የብልፅግና ፓርቲ ጉባኤ የኢትዮጵያን ቀጣይ የፖለቲካና የኢኮኖሚ ፍኖተ ካርታ የሚቀርፅበት ወሳኝ ሁነት እንደሆነ እና ለሀገራዊ ልማት ወሳኝ የሆኑ ቀጣይ ግቦችን እንደሚቀመጡ እምነት እንዳለው በመጥቀስ ለጉባኤው ስኬት መልካሙን ሁሉ መመኘቱን ከብልጽግና ፓርቲ የተገኘው መረጃ አመላክቷል፡፡

የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!

https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation

ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!

Previous article“ብልፅግና ፓርቲ ከጉባኤ እስከ ጉባኤ ያስመዘገባቸውን አመርቂ ውጤቶች ዘላቂነት የሚያረጋግጡ አቅጣጫዎችን ያስቀምጣል” የጉባዔው ተሳታፊዎች
Next articleታጥቀው በጫካ የሚንቀሳቀሱ አካላት ወደ ሰላም በመመለስ የልማቱ አጋዥ እንዲኾኑ የተሀድሶ ሥልጣኞች ጠየቁ።