
ባሕር ዳር: ጥር 23/2017 ዓ.ም (አሚኮ) በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ማዕረግ የዴሞክራሲ ስርዓት ግንባታ ማስተባበሪያ ማዕከል ኀላፊ እና የብልጽግና ፓርቲ ምክትል ፕሬዝዳንት አደም ፋራህ ከሩስያ ዩናይትድ ፓርቲ ሱፕሪም ካውንስል ቢሮ አባልና የሩስያ ፌዴሬሽን ሴናተር አንድሬ ክሊሞቭ ጋር ተወያይተዋል።
የሁለቱን ሀገራት እና የፓርቲ ለፓርቲ ግንኙነት ግንኙነት በሚያጠናክሩ ጉዳዮች ዙሪያ መወያየታቸውን ነው የተመላከተው። በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ማዕረግ የዴሞክራሲ ስርዓት ግንባታ ማስተባበሪያ ማዕከል ኀላፊ እና የብልጽግና ፓርቲ ምክትል ፕሬዝዳንት አደም ፋራህ በፓርቲው አመራርነት ኢትዮጵያ በግብርና፣ በኢንፎርሜሽን ኮሚዩኒኬሽን ቴክኖሎጂ፣ በእንዱስትሪ እና በተለያዩ ዘርፎች ፈጣን ዕድገት ላይ እንደምትገኝ አንስተዋል።
በአረንጓዴ አሻራ በኩል ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥን ለመቋቋም በአህጉርና በዓለምአቀፍ ደረጃ በምታደርጋቸው ጥረቶች ጉልህ ሚና እያበረከተች መኾኗን ተናግረዋል። ባለፉት ዓመታት ሕዝብን በማስተባበር እና በማሳተፍ የተተከሉ በቢሊዮኖች የሚቆጠሩ ችግኞች ማሳያዎች መኾናቸውን ነው ያነሱት።
ኢትዮጵያ የብሪክስ አባል መኾኗ የባለብዙ ወገን ዲፕሎማሲን በማጠናከር ሚናዋን የበለጠ እንድትወጣ እድል የሚሰጥ መኾኑንም ገልጸዋል።
የሩስያ ዩናይትድ ፓርቲ ሱፕሪም ካውንስል ቢሮ አባል እና የሩስያ ፌዴሬሽን ሴናተር አንድሬ ክሊሞቭ በሁለተኛው የብልጽግና ፓርቲ ጉባኤ ላይ እንድንሳተፍ በመጋበዛችን ምስጋና እናቀርባለን ብለዋል። ሁለቱ ሀገራት ዘመናትን የተሻገረ ግንኙነት እንዳላቸው ጠቅሰዋል። ሀገራቱ በንግድ፣ በኢንቨስትመንት በዲፕሎማሲ መስክ ግንኙነታቸውን ይበልጥ ማጠናከር በሚያስችሉ ጉዳዮች መምከራቸውን ገልጸዋል።
ከብልጽግና ፓርቲ የተገኘው መረጃ እንደሚያመላክተው በአቅም ግንባታ መስክም በጋራ ለመሥራትም ከስምምነት ላይ ደርሰዋል።
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!
