
ከሚሴ: ጥር 21/2017 ዓ.ም (አሚኮ) በአማራ ክልል ኦሮሞ ብሔረሰብ አሥተዳደር ለዳልጋ ከብቶች የቅድመ መከላከል ክትባት በዘመቻ መሰጠት ተጀምሯል።
በብሔረሰብ አሥተዳደሩ ደዋ ጨፋ ወረዳ ያገኘናቸው አርሶ አደር መሐመድ ኡመር ክትባት መሰጠቱ የእንስሳቶቻቸውን ጤንነት እንደሚጠብቅላቸው ተናግረዋል።
ሌላው አርሶ አደር አሕመድ ሀሰን ክትባቱ የእንስሳቶቻቸውን ጤንነት ከመጠበቅ ባለፈ የወተት ምርታቸውን እንዲጨምር ያደርጋል ብለዋል።
የኦሮሞ ብሔረሰብ አሥተዳደር እንስሳት እና ዓሳ ሃብት ልማት ጽሕፈት ቤት ኀላፊ ሰይድ ተስፋዬ በሚቀጥሉት ስምንት ቀናት ከ137 ሺህ በላይ የዳልጋ ከብቶችን የቅድመ መከላከል ክትባት ለመስጠት ታስቦ ወደ ሥራ እንደተገባ ተናግረዋል።
በእርጥበት እጥረት ምክንያት አርብቶ አደሮች ከቦታ ወደ ቦታ ስለሚንቀሳቀሱ የእንስሳት በሽታ ወረርሽኝ እንዳይከሰት ክትባቱ አስፈላጊ ኾኖ ተገኝቷልም ነው ያሉት።
የኦሮሞ ብሔረሰብ አሥተዳደር ግብርና መምሪያ ምክትል ኀላፊ ሀሰን ሰይድ ለዳልጋ ከብቶች የሚሰጠው የቅድመ መከላከል ክትባት የእንስሳቱን ጤና በመጠበቅ በግብርናው ዘርፍ እየተሠራ ባለው ተግባር ላይ ምርት እና ምርታማነትን ለመጨመር ከፍተኛ ሚና ይኖረዋል ብለዋል።
ዘጋቢ:- ይማም ኢብራሂም
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
👇👇👇
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን