
ባሕር ዳር: ጥር 19/2017 ዓ.ም( አሚኮ) የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቴዎስ (ዶ.ር) በኢትዮጵያ የደቡብ አፍሪካ አምባሳደር ኢኖንሴባ ሎሲን ዛሬ በጽሕፈት ቤታቸው ተቀብለው አነጋግረዋል።
በውይይታቸውም በሁለትዮሽና አህጉራዊ ጉዳዮች ላይ መክረዋል። የሁለቱን ሀገራት የቆየና ታሪካዊ ግንኙነት የበለጠ ማጠናከር እንደሚገባ አንስተዋል፡፡
ኢትዮጵያና ደቡብ አፍሪካ ጠንካራ የሁለትዮሽ ግንኙነት ያላቸው ሀገራት መኺናቸውን የተናገሩት ሚኒስትሩ አፍሪካ ኀብረትን ጨምሮ በበርካታ ባለብዙ መድረኮች ላይም በትብብር እንደሚሠሩ ገልጸዋል።
የደቡብ አፍሪካ አምባሳደር ኢኖንሴባ ሎሲ ግንኙነቱን ይበልጥ ለማሳደግ እንደሚሠሩ ተናግረዋል። ከሁለትዮሽ ግንኙነት ባሻገር በአፍሪከ ኅብረት፣ በብሪክስ ማዕቀፍ እና በሌሎች ዓለም ዓቀፍ መድረኮች የጋራ ጥቅሞቻቸውን ለማስጠበቅ በትብብር ለመሥራት ፍላጎት እንዳላቸው ገልጸዋል።
ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የተገኘው መረጃ እንደሚያመላክተው በመጭው ወር ለሚካሄደው ለ38ተኛ የአፍሪካ ኀብረት የመሪዎች ጉባኤ ስኬትም በትብብር እንደሚሠሩ አስታውቀዋል።