
ባሕርዳር: ጥር 16/2017 ዓ.ም (አሚኮ) ለመጪው የአፍራካ ኅብረት ጉባኤ የሚሰማሩ ለቪ.አይ.ፒ. አጃቢዎች እና አሽከርካሪዎች ሲወስዱ የነበረውን ሥልጠና አጠናወቀው ዛሬ ተመርቀዋል። በፌደራል ፖሊስ ዋና መሥሪያቤት በተከናወነው ሥነ ሥርዓት የተገኙት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር ብርቱካን አያኖ ጉባኤውን በተሳካ ሁኔታ ለማካሄድ አስፈላጊው ዝግጅት መደረጉን አስታውቀዋል።
ሥልጠናውን የወሰዱ የቪ.አይ.ፒ. አሽከርካሪዎች እና አጃቢዎች የሚሰጣቸውን ስምሪት ሙያዊ ደረጃውን በጠበቀ መስተንግዶ እና በላቀ አገልግሎት መፈፀም እንዳለባቸው አሳስበዋል ።
የፌደራል ፖሊስ ኮሚሽን ኮሚሽነር ጀነራል ደመላሽ ገብረ ሚካኤል ጉባኤውን በአስተማማኝ ጸጥታ እና ደኅንነት ለማከናወን የሚያስችል ካለፉት ጊዜያት የበለጠ ዝግጅት ተደርጓል ብለዋል።
ሥልጠናው የንድፈ ሀሳብ እና የተግባር ተኮር መኾኑን ያነሱት ኮሚሽነር ጄኔራሉ በቅንጅት በመሥራት ለጉባኤው ስኬት የተጣለባቸውን ኀላፊነት እንዲወጡ ማሳሰባቸው ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የተገኘው መረጃ ያመላክታል።
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
👇👇👇
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!
