
ደብረ ብርሃን: ጥር 16/2017 ዓ.ም (አሚኮ) በገጠር መሬት አሥተዳደር እና አጠቃቀም ረቂቅ አዋጅ ላይ በደብረ ብርሃን ከተማ ውይይት እየተደረገ ነው። በመድረኩ ላይ የተገኙት የአማራ ክልል መሬት ቢሮ ምክትል ኀላፊ እብሬ ከበደ ከዚህ በፊት የነበረው የአማራ ክልል መሬት አሥተዳደር እና አጠቃቀም አዋጅ ቁጥር 252/2009 በአዲሱ አዋጅ 1324/2016 የተቀየረ መኾኑን ገልጸዋል።
አዲሱ አዋጅን በተሻለ መንገድ ሥራ ላይ ለማዋል የሃሳብ እና የግብዓት የማሠባሠብ ሥራ እየተሠራ ነው ብለዋል። አዋጁ ከዚህ በፊት በክፍተት ሲነሱ የነበሩ የባለይዞታን መብት እና ተጠቃሚነት የሚያረጋግጥ ስለመኾኑም ነው ያስገነዘቡት። የሰሜን ሸዋ ዞን ምክትል አሥተዳዳሪ ተክለየስ በለጠ ከዚህ በፊት የነበሩ ክፍተቶችን በመለየት በተሻሻለው አዋጅ ላይ ለግብዓትነት የሚውል ውይይት መደረጉንም ነው ያስረዱት።
የደብረ ብርሃን ከተማ አሥተዳደር ምክትል ከንቲባ ወርቃለማሁ ኮስትሬ ውይይት እየተደረገበት ያለው አዋጅ የቅሬታ እና የመልካም አሥተዳደር ችግር ምንጭ የኾኑ ጉዳዮችን ሊያስቀር እንደሚችል ዕምነታቸውን ገልጸዋል።
በውይይቱ ላይ የደብረ ብርሃን ከተማ አሥተዳደር እና የሰሜን ሸዋ ዞን የሥራ ኀላፊዎች፣ የደብረ ብርሃን ዩኒቨርሲቲ እና የሕግ አካላት ተሳትፈዋል።
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
👇👇👇
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!
