
ጎንደር: ጥር 10/2017 ዓ.ም (አሚኮ) የኢፌዴሪ ፕሬዚዳንት ታዬ አጽቀ ሥላሴ በጥምቀት በዓል ላይ ለመታደም ጎንደር መግባታቸውን መዘገባችን ይታወሳል። ፕሬዚዳንቱ ከጎንደር ከተማ የተለያዩ የማኅበረሰብ ተወካዮች ጋር ተወያይተዋል።
በውይይቱ የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈ ጉባኤ አገኘሁ ተሻገር፣ የአማራ ክልል ርእሰ መሥተዳድር አረጋ ከበደን ጨምሮ ከፍተኛ የመንግሥት የሥራ ኀላፊዎች ተሳታፊ ኾነዋል።
ጎንደር ጥንታዊ፣ ታሪካዊ እና የጥበብ ከተማ ናት ሲባል ማሳያዎቿ ሕያው ናቸው ያሉት የኢፌድሪ ፕሬዚዳንት ታዬ አጽቀ ሥላሴ መጠበቅ፣ መንከባከብ እና ማስቀጠል የዚህ ትውልድ ታሪካዊ ግዴታ ነው ብለዋል።
በየዘመኑ የሚከሰት ልዩነት እና አለመግባባት ተፈጥሯዊ ክስተት እንደኾነ ያነሱት ፕሬዚዳንቱ “ጥንታዊ ሥልጣኔን ታሳቢ ያደረገ፣ ታሪክን ከግምት ያስገባ እና እሴትን የጠበቀ የሃሳብ ልዕልና ያስፈልጋል” ነው ያሉት።
የማኅበረሰብ ተወካዮቹ ጎንደር ከተማን የሚመጥኑ እና የተጀመሩ የልማት ፕሮጀክቶች መኖራቸውን አንስተዋል። የፌደራል እና የክልሉ መንግሥት በችግር ውስጥም ኾነው ፕሮጀክቶቹን ለማጠናቀቅ ያላቸው ቁርጠኝነት ተስፋ ሰጪ ነው ብለዋል። በከተማዋ ብሎም በክልሉ አሉ ያሏቸውንም ጥያቄዎች አንስተው ውይይት አድርገዋል።
ዘጋቢ፦ ታዘብ አራጋው
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
👇👇👇
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!