
አዲስ አበባ: ታኅሣሥ 28/2017 ዓ.ም (አሚኮ) ብጹዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት ለልደት በዓል የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክት አስተላልፈዋል። በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን አማኞች ዘንድ በድምቀት የሚከበረው የኢየሱስ ክርስቶስ የልደት በዓልን አስመልክቶ መግለጫ የሰጡት ብጹዕነታቸው “የእግዚአብሔርን መንገድ መከተል ሰላምን ጨምሮ መልካም ነገርን ሁሉ ወደ እኛ ያመጣል” ብለዋል።
በኢትዮጵያ ብሎም በዓለም ለምናያቸው የሰላም መደፍረሶች ምንጫቸው ፈጣሪን አለመፍራት እንደኾነ ተናግረዋል። ብጹዕነታቸው የ2017 ዓ.ም የልደት በዓል ሲከበርም ፍቅርን፣ እርቅን እና ሰላምን ለማኅበረሰቡ የማስረጽ አጀንዳን ይዘን ሊኾን ይገባል ብለዋል በመግለጫቸው። ወደልባችን ተመልሰን በፍቅር እና በወንድምነት ወደሚገኝ አንድነት መምጣት እንደሚያስፈልግም ገልጸዋል።
አማኙ በዓሉን ካለው ላይ ከፍሎ ለተፈናቃይ ወገኖች እና ለአቅመ ደካሞች በመለገስ በመንፈሳዊ ደስታ እና ሰላም እንዲያከብርም መልዕክት አስተላልፈዋል።
ዘጋቢ፦ ቤተልሄም ሰለሞን
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
👇👇👇
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!