
ባሕር ዳር: ታኀሣሥ 18/2017 ዓ.ም (አሚኮ) ለውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ሠራተኞች እና በጎ ፈቃደኞች በአፍሪካ አመራር ልህቀት አካዳሚ ሲሰጥ የነበረውን የ10 ቀን ሥልጠና ዛሬ ተጠናቅቋል። በሥልጠናው ማጠናቀቂያ ላይ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቲዎስ (ዶ.ር)፣ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ድኤታ አምባሳደር ብርቱካን አያኖ፣ የመንግስት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት ሚኒስትር ድኤታ ተስፋሁን ጎበዛይ እና የውጭ ጉዳይ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ጃፋር በድሩ ተገኝተዋል።
ሥልጠናውን የሰጡት የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴርን ጨምሮ የተለያዩ ሚኒስትሮች እና የተለያዩ ተቋማት አመራሮች ናቸው። ሥልጠናው በአዲስ አበባ በየካቲት 2017 ዓ.ም በሚካሄደው 38ኛው የአፍሪካ ኅብረት የመሪዎች ጉባዔ እና 46ኛው የኅብረቱ የሥራ አሥፈጻሚ ምክር ቤት መደበኛ ስብሰባ ላይ ያተኮረ ነው።
የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቲዎስ (ዶ.ር) በጎ ፈቃደኞች ኢትዮጵያ በአፍሪካ የዲፕሎማሲ ማዕከልነቷ እየተወጣች ያለውን ሚና ለመደገፍ ላሳዩት ቁርጠኝነት ምስጋናቸውን አቅርበዋል።
የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ድኤታ አምባሳደር ብርቱካን አያኖ በአዲስ አበባ የሚካሄደው የአፍሪካ ኅብረት ጉባዔ ስኬታማ እንደሚኾን ያላቸውን እምነት ስለመግለጻቸውም የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር መረጃ ያመለክታል።
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
👇👇👇
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!