
ባሕር ዳር: ታኅሳስ 14/2017 ዓ.ም (አሚኮ) በኦሮሚያ ክልል ሆሮ ጉዱሩ ዞን የተጀመረው ሰላማዊ እንቅስቃሴ ተጠናክሮ እንዲቀጥል የሚደግፍ ሕዝባዊ ሰላማዊ ሰልፍ ተካሂዷል፡፡ በሕዝባዊ ሰልፉ ከክልሉ መንግሥት ጋር ስምምነት በመፈጸም ሰላም እንዲሰፍን ቁርጠኝነታቸው ላሳዩ የታጠቁ ኃይሎች ምስጋና ቀርቧል።
በጫካ የሚገኙ ታጣቂዎችም ለመንግሥት የሰላም ጥሪ ምላሽ በመስጠት ወደ ካምፕ በመግባት ሰላማዊ አማራጭን እንዲከተሉ ጥሪ ተላልፏል። ሕዝብ በሰላም እጦት ምክንያት በዘርፍ ብዙ ችግሮች ውስጥ መኾኑንም ሰልፈኞቹ አንስተዋል፡፡
በጫካ የቀሩ ታጣቂዎች የሕዝብን እና የመንግሥትን የሰላም ጥሪን ማክበር እንደሚገባቸው ነው ያነሱት፡፡ “ለኦሮሞ ሕዝብ መታገል የማኅበረሰቡን ፍላጎት ማሟላት ነው” ያሉት ሰልፈኞቹ ጠመንጃ መፍትሄ አያመጣም ብለዋል፡፡ ኤፍ ኤም ሲ እንደዘገበው ልዩነቶችን በምክክር መፍታት እንደሚገባ ተናግረዋል፡፡
ዘላቂ ሰላም እንዲረጋገጥ የሚጠይቁ መፈክሮችም በሕዝባዊ ሰልፉ ላይ ተላልፈዋል። በሰልፉ ላይ አባገዳዎች፣ ሀደ ስንቄዎች፣ የሀገር ሽማግሌዎች፣ የሃይማኖት አባቶችን እና ሌሎች ተሳትፈዋል፡፡
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
👇👇👇
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!