
ባሕር ዳር: ታኅሣሥ 09/2017 ዓ.ም (አሚኮ) የብልጽግና ፓርቲ ምክትል ፕሬዚዳንት አደም ፋራህ ዛሬ በመላው አማራ ክልል የተካሄዱ ሕዝባዊ የሰላም ሰልፎችን አስመልክተው በማኅበራዊ ትስስር ገጻቸው የሚከተለውን መልእክት አስተላልፈዋል።
ዛሬ በአማራ ክልል የተለያዩ ከተሞች ሕዝቡ በነቂስ በመውጣት በክልሉ ሰላም እንዲሰፍን፣ የሕግ የበላይነት እንዲከበር፣ በንፁሃን ላይ ግፍ እየፈፀሙ የሚገኙ ጽንፈኛ ኃይሎች ለሕግ እንዲቀርቡ፣ መንግሥት በተደጋጋሚ እያቀረበ ለሚገኘው የሰላም ጥሪ ድጋፍ እንደሚቸር በይፋ ድምፁን አሰምቷል፤ እጅግ በጣም እናመሰግናለን!
በቀጣይም ክልሉ በተሟላ ሁኔታ ዳግም ወደ ሰላማዊ እንቅስቃሴ እንዲመለስ በብልፅግና ፓርቲ የሚመራው መንግሥት ኅብረተሰቡን በማሳተፍ ያላሰለሰ ጥረት ማድረጉን የሚቀጥል ይኾናል። በመንግሥት በኩል ለሰላም፣ ለውይይት እና ድርድር የምትጠልቅ ጀምበር እንደሌለችም ደጋግመን ማረጋገጥ እንወዳለን።
ስለኾነም በአማራ ክልል ታጥቀው የሚንቀሳቀሱ አካላት በኃይል አማራጭ የሚገኝ መፍትሔ አለመኖሩን በመረዳት በዛሬው ሰልፍ ጨምሮ ሕዝቡ በተደጋጋሚ እያነሳቸው ያሉ ጥያቄዎች ምላሽ እንዲያገኙ፣ በተለያዩ የሀገራችን አከባቢዎች እየታየ እንደሚገኘው በአስቸኳይ ወደ ሰላማዊ እንቅስቃሴ እንዲመለሱ ጥሪያችንን እናቀርባለን።
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
👇👇👇
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!