
ደሴ: ታኅሣሥ 09/2017 ዓ.ም (አሚኮ) በደቡብ ወሎ ዞን በጊምባ ከተማ አሥተዳደር ሕዝባዊ የድጋፍ ሰልፍ ተካሂዷል። በሰልፉ ላይ ተማሪዎች፣ የሀገር ሽማግሌዎች፣ የሃይማኖት አባቶች እንዲሁም የከተማዋ ነዋሪዎች ተሳትፈዋል።
ነዋሪዎቹ በመልዕክታቸው ክልላችን በጦርነት ውስጥ መቆየት የለበትም፣ ለሕዝብ እንታገላለን የሚሉ ኀይሎችም ለንግግር እና ለውይይት ቅድሚያ እንዲሰጡ ጠይቀዋል።
በጦርነቱ ምክንያት የኑሮ ውድነት ኅብረተሰቡን እየፈተነው እንደሚገኝ የገለጹት ነዋሪዎቹ፤ ልዩነቶችን በውይይት በመፍታት ሰላም እንዲሰፍን መልዕክት አስተላልፈዋል።
የሰልፉ ተሳታፊ ተማሪዎችም “ደብተር እና እስክርቢቶ እንጂ የጥይት ድምጽ መስማት አንፈልግም” ብለዋል። ትምህርት ያልተጀመረባቸው አካባቢዎችም ወደ ሥራ እንዲገቡ ጠይቀዋል።
የጊምባ ከተማ አሥተዳደር ከንቲባ እያሱ ዓባይ አሁን ላይ በክልሉ እየተስተዋለ ያለው ጦርነት የሕዝብን ችግር የሚያባብስ መኾኑን ገልጸዋል። በመኾኑም መንግሥት በተደጋጋሚ እያደረገ ያለውን የሰላም ጥሪ በመቀበል ግጭት ሊቆም እንደሚገባ ተናግረዋል።
በጊንባ ከተማ የተለያዩ መልክቶች የተላለፉበት ሕዝባዊ የድጋፍ ሰልፍ በሰላም ተጠናቋል።
ዘጋቢ:- ተመስገን አሰፋ
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
👇👇👇
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!