
አዲስ አበባ: ኅዳር 28/2017 ዓ.ም (አሚኮ) 19ኛው የብሔር ብሔረሰቦች እና ሕዝቦች በዓል ሲምፖዚየም በአርባ ምንጭ ከተማ እየተካሄደ ነው። የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈ ጉባኤ አገኘሁ ተሻገር ሁሉም የክልል ርእሰ መሥተዳድሮች እና የሁለቱ ከተማ አሥተዳደር ከንቲባዎች በተገኙበት ሲምፖዚየም ላይ መልእክት አስተላልፈዋል።
ባለፉት ዓመታት በዓሉ ሲከበር ብሔር ብሔረሰቦች ከልዩነት ይልቅ አንድነት እና መተሳሰብን የሚያጎላ ነው ብለዋል። ሀገር ለማስቀጠል ኅብረ ብሔራዊነትን እና አንድነትን አስጠብቀን ሀገር የማስቀጠል ግዴታ አለብን ነው ያሉት።
የትኛውንም ግጭት እና አለመግባበት ለመፍታት ሰላማዊ አማራጭ መከተል በየትኛውም ሁኔታ አስፈላጊ መሆኑን አንስተዋል። ግጭቶችን በሰላም ለመፍታት በክልሎች መካከል የተጀመረው የበይነ መንግሥታት ግንኙነት አካሔድን በአግባቡ መተግበር ይገባል ብለዋል።
ዲሞክራሲያዊ አንድነት እና ሀገረ መንግሥት እንዲጸና ሰላም እጅግ ወሳኝ በመሆኑ ብሔር ብሔረሰቦች ለዚህ ሰላም በትብበር መሥራት ይገባል ሲሉ ተናግረዋል። እንደ አድዋ እና ህዳሴ ግድብ ያሉ ከታሪክ የማይፋቁ አሻራዎችን ለማስቀመጥ አብሮነትን በማስቀጠል ሀገራዊ አንድነትን ማስጠበቅ ያስፈልጋል ብለዋል አፈጉባኤው።
ዘጋቢ ፦ አንዱዓለም መናን – ከአርባምንጭ
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!