
ደብረ ብርሃን: ኅዳር 22/2017 ዓ.ም (አሚኮ) በደብረ ብርሃን ከተማ የሚሊሻ ሥልጠና ማስጀመሪያ መርሐ ግብር ተካሂዷል።
የሥልጠናው ዋነኛ ዓላማ የሕዝብን ደኅንነት ማረጋገጥ ነው ተብሏል። የደብረ ብርሃን ከተማ አሥተዳደር ሰላም እና ጸጥታ መምሪያ ኀላፊ ዳንኤል እሸቴ የአካባቢን ሰላም ለማስጠበቅ ሥልጠናውን በብቃት መወጣት ይገባል ሲሉ ለሠልጣኞች መልዕክት አስተላልፈዋል።
በደብረ ብርሃን ከተማ የጸጥታ ካውንስል አባል ብርጋዴር ጄኔራል ጠቅለው ክብረት የክልሉን ሰላም እና ጸጥታ ለማረጋገጥ መዋቅሩን ማጠናከር አስፈላጊ መኾኑን አንስተዋል። ለዚህም ሠልጣኞች የሚሰጣችሁ ሥልጠና ላይ ትኩረት ማድረግ አለባችሁ ሲሉ መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል።
የደብረ ብርሃን ከተማ አሥተዳደር ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ በድሉ ውብሸት በከተማዋ ያለው የዕድገት ግለት እንዳይቀጥል የሚያደርግ ሂደት አጋጥሞ መቆየቱን አስረድተዋል።
ችግሩን ለመቀልበስ ሰፊ ጥረት ተደርጓል ያሉት ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባው ዘላቂነት እንዲኖረው የተደራጀ የጸጥታ ኀይል ያስፈልጋል ነው ያሉት።
ሥልጠናው ስኬታማ እንዲኾን ከተማ አሥተዳደሩ ሁሉን አቀፍ ድጋፍ ያደርጋልም ብለዋል።
የከተማዋን ብሎም የቀጣናውን ሰላም ለማስጠበቅ የሚደረገውን ተግባር ሊደግፍ የሚያስችል የሚሊሻ ሥልጠና ዛሬ ስለመጀመሩም ተገልጿል።
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!