
ደብረ ማርቆስ: ኅዳር 18/2017 ዓ.ም (አሚኮ) በምሥራቅ ጎጃም ዞን ደብረ ማርቆስ ከተማ አሥተዳደር ከከተማው ነዋሪ ሴቶች ጋር ሰላምን አስመልክቶ ውይይት ተካሂዷል፡፡ ወጣት ብርቱካን ይሄነው የደብረ ማርቆስ ከተማ ነዋሪ ናት። በተፈጠረው የሰላም እጦት ምክንያት ወላጅ አባቷን አጥታለች፡፡በዚህ ምክኒያት ቤተሰባቸው ለዘርፈ ብዙ ችግር እንደተጋለጠ ተናገራለች፡፡
ሰላም ለሁሉም መሰረት ነው የምትለው ብርቱካን የተፈጠረው ቀውስ ወደ ሰላም ይመጣ ዘንድ ሁሉም የበኩሉን ድርሻ ሊወጣ እንደሚገባ ገልጻለች፡፡ የሰላም እጦቱ በሴቶች ላይ ዘርፈ ብዙ ችግር እያደረሰ መኾኑን የተናገሩት የውይይቱ ተሳታፊዎች ዘላቂ ሰላም እንዲመጣ ሴቶች ኀላፊነታችንን ልንወጣ ይገባል ብለዋል፡፡
የከተማ አሥተዳሩ ብልጽግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት የአደረጃት ዘርፍ ኀላፊ ወይዘሮ ላቀች ሰማ በተፈጠረው የሰላም እጦት ሴቶች በከፍተኛ ደረጃ የችግሩ ሰለባ መኾናቸውን ተናግረዋል። ዘላቂ ሰላም እንዲረጋገጥ ከመነጋገር እና ከመመካከር ባለፈ የተግባር ሥራዎችን መሥራት እንደሚገባ አሳስበዋል።
የደብረ ማርቆስ ከተማ አሥተዳደር ሴቶች ሕጻናት እና ማኅበራዊ ጉዳይ መምሪያ ኀላፊ ወይዘሮ ፈንታነሽ አፈወርቅ የሰላም እጦቱ በሴቶች እና ህጻናት ላይ የሚያደርሰው ጫና ከፍተኛ መኾኑን ተናግረዋል። በከተማ አሥተዳደሩ ዘላቂ ሰላም ከማምጣት ባለፈ ሴቶችን በኢኮኖሚያዊ እና ማኅበራዊ ዘርፎች ተጠቃሚ ለማድረግ እየተሠራ መኾኑን ገልጸዋል፡፡
ዘላቂ ሰላም እንዲመጣም ሁሉም የማሕበረሰብ ክፍል ድርሻውን ሊወጣ እንደሚገባም አሳስበዋል።
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
👇👇👇
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!