
ባሕር ዳር: ኅዳር 17/2017 ዓ.ም (አሚኮ) ሀገራዊ ምክክር በኢትዮጵያ ውስጥ እንዲካሄድ ሁለት መነሻ ምክንያቶች እንዳሉ የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ገልጿል።
በኢትዮጵያ ውስጥ በሚገኙ የሃሳብ መሪዎች እንዲሁም የኅብረተሰብ ክፍሎች መካከል መሠረታዊ በኾኑ ሀገራዊ ጉዳዮች ላይ የሃሳብ ልዩነት እና አለመግባባት መኖሩ ሀገራዊ ምክክር ለማካሄድ እንደ ገፊ ምክንያት እንደሚታይ ነው የገለጸው።
የምክክር ኮሚሽኑ ለዘመናት ሲንከባለሉ የመጡ ውስጣዊ ችግሮችን በውይይት ለመፍታት የሚያስችል የፖለቲካ ባሕል ለማዳበር እና ለዲሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታ ምቹ መደላድል ለመፍጠር ሀገራዊ ምክክሩ አስፈላጊ ስለመኾኑም ነው ያብራራው።
ከሌሎች ሀገራት ልምድ በመነሳት እና የሀገሪቱን ነባራዊ ሁኔታ በማጥናት በኢትዮጵያ የሚደረገው ሀገራዊ ምክክር የሁሉንም ባለድርሻ አካላት ተሳትፎ እንደሚጠይቅም አንስቷል።
ኮሚሽኑ የሚስተዋሉትን ሰፋፊ እና ዘርፈ ብዙ ልዩነቶችን ለመፍታት አካታች የሕዝብ ምክክሮችን ማድረግ አስፈላጊ ኾኖ በመገኘቱ ይህንም ለማስጀመር ወደ ሥራ ተገብቷል ነው ያለው።
ምክክሩ የሀገሪቱን ጥቅም ማስቀደምን እና ሀገር በቀል ዕውቀቶችን መጠቀምን እንደ መሠረታዊ መርሆዎቹ አድርጎ ስለሚወስድ ሂደቱን ከውጭ ተፅዕኖ ነፃ እንዲኾን ያደርገዋል ሲል የሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ባወጣው መረጃ አስፍሯል።
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!