
ደብረ ብርሃን:ኅዳር 14/2017 ዓ.ም (አሚኮ) የደብረ ብርሃን ጤና ጣቢያ አገልግሎቱን በተሻለ ሁኔታ ተደራሽ ለማድረግ ያስችለው ዘንድ ባለ ሦስት ወለል ህንጻ ገንብቶ ለአገልግሎት ክፍት አድርጓል፡፡
የአማራ ክልል ጤና ቢሮ ኀላፊ አብዱከሪም መንግሥቱ ጤና ተቋማትን ማስፋፋት እና ማዘመን የትውልድ ቅብብሎሽን ማስቀጠል ነው ብለዋል።
የማኅበረሰቡን የጤና አገልግሎት ለማረጋገጥ የጤና መሠርተ ልማትን ተደራሽ ለማድረግ የሚሠራው ሥራ በደብረ ብርሃን ከተማ ውጤቱ ታይቷል ነው ያሉት።
የደብረ ብርሃን ከተማ አሥተዳደር ተቅዳሚ ምክትል ከንቲባ በድሉ ውብሸት ውጤታማ የጤና አገልግሎት ለተገልጋዮች ለማድረስ የአቻ ተቋማት እገዛ እና የመሪዎች ቁርጠኝነት ትልቅ ሚና አለው ብለዋል።
በከተማው በሚገኙ ጤና ተቋማት ጥራት ያለው እና ቀልጣፋ አገልግሎት ለመስጠት በተደረገው ጥረት ለተገልጋዮች እርካታን የጨመሩ ሥራዎች መኖራቸውን የደብረ ብርሃን ከተማ አሥተዳደር ጤና መምሪያ ኀላፊ በቀለ ገብሬ ገልጸዋል፡፡
በጤና ጣቢያ ደረጃ የእናቶች ወሊድ ቀዶ ሕክምና አገልግሎት እና ከወረቀት ንክኪ ነጻ የመድኃኒት ቤት አገልግሎት መጀመሩን የመምሪያው ኀላፊ በቀለ ገብሬ ተናግረዋል።
ዘጋቢ፡- ለዓለም ለይኩን
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!