
ባሕር ዳር: ኅዳር 01/2017 ዓ.ም (አሚኮ)የጎግል ፕሌይ (Google Play) አልሚዎች ምዝገባ ኢትዮጵያውያን አልሚዎችን መቀበል መጀመሩን የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር አስታውቋል፡፡ የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር በለጠ ሞላ (ዶ.ር) እንደገለጹት የጎግል ፕሌይ የአልሚዎች ምዝገባ ኢትዮጵያውያን አልሚዎችን መቀበል መጀመሩ ለኢትዮጵያ የዲጂታል ኢኮኖሚ ግንባታ ትልቅ ተጽዕኖ የሚፈጥር ነው፡፡
ይህ ምዕራፍ የሀገር ውስጥ የቴክኖሎጂ ተሰጥኦ ባለቤቶች መተግበሪያዎቻቸውን በዓለም ካሉት ትላልቅ ዲጂታል መድረኮች ላይ እንዲያትሙ አዲስ እድሎችን እንደሚከፍት አንስተዋል፡፡
መንግሥት የዲጂታል ኢኮኖሚውን ለመገንባት በርካታ ተነሳሽነቶችን በመተግበር እየሠራ መኾኑን ጠቁመዋል። ይህ አዲስ ጅማሮ የተከናወኑ ተግባራት ውጤት ነው ብለዋል።
ይህንን እድል ተጠቅመው የዘርፉ ባለሙያዎች ችግር ፈቺ መተግበሪያዎችን በማልማት በዲጂታል ኢኮኖሚ ግንባታ ሒደት የድርሻቸውን እንደሚወጡም ጥሪ አቅርበዋል።
ሚኒስቴሩ እንደገለጸው እድሉ ኢትዮጵያውያን አልሚዎች የጎግል ፕሌይን ዓለም አቀፍ ታዳሚዎች በቀጥታ በማስገኘት መተግበሪያዎቻቸው ሰፊ እይታን እንዲያገኙና ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪ እንዲሆን ያግዛል፡፡
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!