
ደብረ ብርሃን: ጥቅምት 27/2017 ዓ.ም (አሚኮ) በሰሜን ሸዋ ዞን ሀገረ ማርያም ወረዳ በሰላም እና ጸጥታ ዙሪያ ከሕዝቡ ጋር ውይይት ተደርጓል። በውይይቱ የሰሜን ሸዋ ዞን አሥተዳዳሪ መካሻ ዓለማየሁ ማኅበረሰቡ ከግጭት ያገኘው ትርፍ ሳይኾን ጉዳት እንደኾነ ተገንዝቧል ብለዋል።
በዚህ ምክንያት ለሰላም ያለው ውግንና እየጨመረ መጥቷል ያሉት አቶ መካሻ ከሰላም የሚጠቀመው ሁሉም እንደኾነ ታምኖ ማኅበረሰቡ ለሰላም እንዲሠራም አሳስበዋል። ተሳታፊዎቹ በሰላም እጦቱ ምክንያት በኢኮኖሚ፣ በማኅበራዊ እና በሥነ ልቦና ደረጃ እየደረሰ ያለው ተጽዕኖ ከባድ እንደኾነ አንስተዋል።
ዛሬ ላይ ተማሪዎች አልተማሩም ማለት የነገዋን ሀገር በዕውቀት የሚመራ ትውልድ እንደማይኖር ሊታወቅ ይገባል ብለዋል። የእስካሁኑ ችግር አብቅቶ ፊትን ወደ ሰላም በማዞር ራስን ዝግጁ ማድረግ እንደሚገባም አሳስበዋል።
በሀገር መከላከያ ሠራዊት የኮማንዶ እና አየር ወለድ እዝ አዛዥ ሌተናል ጄኔራል ሹማ አብደታን ጨምሮ የሰሜን ሸዋ ዞን ከፍተኛ የሥራ ኀላፊዎች በውይይቱ ታድመዋል፡፡
ዘጋቢ፡- ለዓለም ለይኩን
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!